የተጣሩ መረጃዎች

ሀሰት፡ ምስሉ በኦሮሚያ ክልል ወለጋ ውስጥ የተገደሉ የአማራ ብሄር ተወላጆችን አያሳይም

በኅዳር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ከ7 ሺህ በላይ ተከታዮች ያሉት የፌስቡክ ገፅ የአማራ ብሄር ተወላጆች በኦሮሚያ ክልል ወለጋ ላይ እየተገደሉ ነው በማለት አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። 

ይህ የፌስቡክ ገጽ በአያያዘው ምስል ላይ “በኦሮሚያ ክልል የአማራ ተወላጆች ላይ እየተፈፀመ ያለ ዘር ማጥፋት” የሚል ፅሁፍ አድርጎበታል። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ39 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ኢትዮጵያ በተለያዩ የእርስ በርስ ግጭቶች እና አለመረጋጋቶች ውስጥ እያለፈች ትገኛለች። በእነዚህ ጊዜያቶችም ውስጣዊ የድንበር ግጭቶች ፤ የብሄር ግጭት ፤ ሞት እና መፈናቀሎችም ተከስተዋል።

ከነዚህ ክስተቶች መሃልም በሰሜኑ የሀገሪቷ ክፍል በህወሓት እና በፌደራል መንግስት መካከል ተከስቶ የነበረው እና ለሁለት አመት ቆይቶ የነበረው የእርስ በርስ ጦርነት ይጠቀሳል።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በምዕራብ ኦሮሚያ ወለጋ ውስጥ በተከሰተው ግጭት ምክንያት በተደጋጋሚ የተለያዩ የጅምላ ግድያዎች ፤ ሞት እና መፈናቀሎች እየተሰሙ ይገኛሉ።

በዚህም ግጭት ምክንያት ንፁሃን የአማራ እና ኦሮሞ ተወላጆች የዚህ ግጭት ሰለባ ሆነዋል። የዜና ሪፖርቶች በነዚህ ግጭት በተባባሰባቸው አካባቢዎች የአማራ ብሄር ተወላጆች እንደሚገደሉ እና እንደሚፈናቀሉ ያሳያሉ። 

ይህን የሰዎች ሞት እና መፈናቀልን ተከትሎ መንግስት ድርጊቱን የፈፀመው ኦነግ ሸኔ ነው ቢልም ኦነግ ሸኔ በተቃራኒው ነገሩን ሲያስተባብልና መንግስትን ሲከስ ቆይቷል።      

ይህ የፌስቡክ ፖስትም በዚህ ሀሳብ ላይ መሰረት አድርጎ የተጋራ ነው።  

ሀቅቼክ ባደረገው ማጣራት መሠረት ምስሉ የቆየ እና በሐምሌ 2012 ዓ.ም በአንድ የዜና ድረገፅ ላይ ተጋርቶ የነበረ ነው። 

ምስሉ ለመጀመርያ ግዜ በአንድ የዜና ድረገፅ ላይ የተጋራ ሲሆን፤ ሁለት የሶማልያ ወታደሮች በደቡብ ምዕራብ ሶማልያ በምትገኘው እና ባይዶአ ተብላ በምትጠራው አካባቢ የ10 አመት ወንድ ልጅ ላይ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል መፈፀማቸውን ተከትሎ በአደባባይ ተሰቅለው በጥይት እንደተገደሉ የሚያሳይ እንደሆነ ማረጋገጥ ተችሏል።
 

ከዚህ በተጨማሪም ይህ የዜና ምንጭ ሁለቱ ወታደሮች በሶማልያ የ60ኛ ክፍለ ጦር ወታደሮች በጥይት ተመተው ከመገደላቸው በፊት በከተማዋ ውስጥ ታስረው ሲዞሩ እና በህዝብ ፊት ሲታዩ እንደነበረ ዘግቧል።
ስለዚህ ሀቅቼክ ይህ የፌስቡክ ፖስት የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ሀሰት፡ ምስሉ በኦሮሚያ ክልል የአማራ ክልል ተወላጆች ላይ እየተፈፀመ ያለ እስርን አያሳይም

በታህሳስ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ላይ ከ64 ሺህ በላይ ተከታዮች ያሉት አንድ የፌስቡክ ገፅ “ወለጋ ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሸባሪ ብሎ የፈረጀውን  ኦነግ ሸኔን ለምን ተጋጠማችሁ ብሎ አማሮችን የኦሮሚያ ልዩ ኃይል ማሰር ጀምሯል።” የሚል የመግለጫ ፅሁፍን በማያያዝ አንድ ምስል አያይዞ አጋርቶ ነበር። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከ130 በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ30 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የኦሮሚያ ክልል ልዩ ሀይሎች የአማራ ተወላጆችን ማሰር ጀምረዋል ተብሎ የተጋራው ምስል ትክክለኛነት አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።

የፌደራሉ መንግስት እራሱን የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት ብሎ ከሚጠራው እና በሌሎች ደግሞ ኦነግ ሸኔ እየተባለ ከሚጠራው አካል ጋር ጦርነት ውስጥ እንደገባ የሚያሳዩ መረጃዎች እየወጡ ቆይቷል። በሁለቱ አካላት መካከል የተከሰተው ግጭት ከጊዜ ወደ ጊዜ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ እየተስፋፋ መጥቷል። 

በዚህ ግጭት ምክንያት በኦሮሚያ ክልል በተለይም በወለጋ አካባቢ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሲሞቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ደግሞ ከመኖሪያ ቀዬአቸው ተፈናቅለዋል።  

የፌደራሉ መንግስት በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ከኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ጋር ተከታታይ የሆነ ግጭት እና ጦርነት ውስጥ እንደሆነ የሚያሳዩ ሪፖርቶች ሲወጡ ቆይተዋል። ይህ በዋነኝነት በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ አካባቢ በሁለቱ አካላቶች መካከል የተከሰተው ግጭት በክልሉ ብቻ ሳይሆን በአጎራባች አካባቢዎችም ላይ መጠነ ሰፊ የሆነ አለመረጋጋት ፣ የሰው ሞት እና መፈናቀልን እያመጣ ይገኛል።

የፌደራሉ መንግስት እንዲሁም የኦሮሚያ ክልል መንግስት በክልሉ ውስጥ ለሚፈጠሩ የሰው ልጅ ሞት እና መፈናቀሎች ተጠያቂው የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ናቸው ብለው ሲገልፁ በተቃራኒው ደግሞ ኦነግ ሸኔ ንፁሃን ላይ ለሚደርሰው ጥቃት ተጠያቂው እራሱ መንግስት ነው ሲል ሲከስ ይደመጣል

አዲስ ስታንዳርድ የተሰኘው የሀገር ውስጥ ጋዜጣ የአይን ምስክሮች ነገሩኝ ብሎ ባጋራው መረጃ መሰረት  በህዳር ቀን 16 እና 20 2015 ዓ.ም ላይ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ኪረሙ ወረዳ ውስጥ የአማራ ክልል ፋኖ ታጣቂዎች ብዙ ሰው መግደላቸውን ዘግቧል።  

በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን አካባቢ ግጭቶች የነበሩ ሲሆን የተከሰተው ግጭትም የብዙ ንፁሀንን ህይወት ቀጥፏል።  በዚህም ግጭት የተነሳ ከ30 ሺህ በላይ የሚሆኑ የአማራ እና የኦሮሞ ተወላጆች ከመኖሪያ ቦታቸው እንደተፈናቀሉ የሚያሳዩ መረጃዎች ወጥተው ነበር፡፡

በዚህ የፌስቡክ ገፅ ላይ የተሰራጨው ይህ መረጃም በዚህ ሀሳብ ላይ ተመስርቶ ነው።

ሀቅቼክ መረጃውን ለመደገፍ የተጋራውን ምስል ለማጣራት ባደረገው ጥረት መሰረት ምስሉ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጋራው ሚያዝያ 16 ቀን 2012 ዓ.ም በቢቢሲ የኦሮምኛ ቋንቋ እትም ላይ ሲሆን በቢቢሲ ዘገባ መሰረት ምስሉ በኦሮሚያ ክልል ጅማ ዞን አብዶ አባ ጆቢር የተባለ መምህር በክልሉ ልዩ ሀይሎች በቁጥጥር ስር መዋሉን የሚያሳይ እንደሆነ ማረጋገጥ ተችሏል።

በዚህም ምክንያት ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ሀሰት፡ ምስሉ በቤንሻንጉል ክልል በኦሮሚያ ልዩ ሀይሎች እና በኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች አማካኝነት የሚቃጠል የአማራ ተወላጆችን ቤት አያሳይም

በታህሳስ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ላይ ከ20ሺህ በላይ ተከታይ ያለው አንድ የፌስቡክ ገፅ “በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካማሺ ዞን ሚዥጋ ወረዳ መንደር 42/ተንካራ ላይ ታህሳስ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ከረፋዱ 4 ሰዓት ጀምሮ  ከአርጆ ጉደቱ በመነሳት ወረራ የፈጸመው መንግስት መሩ የኦሮሚያ ልዩ ኃይል እና አሸባሪው ኦነግ ሸኔ ሰላማዊ አማራዎችን በጅምላ በማጥቃት መኖሪያ ቤቶችን እያቃጠለ እና እየዘረፈ ነው።”  የሚል የመግለጫ ፅሁፍን በማያያዝ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከ190 በላይ ግብረመልስን ሲያገኝ ከ30 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ይህ የፌስቡክ ፖስት መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።

የፌደራሉ መንግስት በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ከኦነግ ሸኔ ትጣቂዎች ጋር ተከታታይ የሆነ ግጭት እና ጦርነት ውስጥ እንደሆነ የሚያሳዩ ሪፖርቶች ሲወጡ ቆይተዋል። ይህ በዋነኝነት በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ አካባቢ በሁለቱ አካላቶች መካከል የተከሰተው ግጭት በክልሉ ብቻ ሳይሆን በአጎራባች አካባቢዎችም ላይ መጠነ ሰፊ የሆነ አለመረጋጋት ፣ የሰው ሞት እና መፈናቀል እየተፈጠረ ይገኛል።

የፌደራሉ መንግስት እና የኦሮሚያ ክልል መንግስት በክልሉ ውስጥ ለሚፈጠሩ የሰው ልጅ ሞት እና መፈናቀል ተጠያቂው የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ናቸው ብለው ሲገልፁ በተቃራኒው ደግሞ ኦነግ ሸኔ ንፁሃን ላይ ለሚደርሰው ጥቃት ተጠያቂው እራሱ መንግስት ነው ሲል ሲከስ ይደመጣል

በቤንሻንጉል ክልል ካማሺ ዞን እና አካባቢው ተከታታይ የሆኑ ግጭት ፣ ሞት እና መፈናቀሎች ሲከሰቱ የቆዩ ሲሆን ይህ አካባቢም ከኦሮሚያ ክልል ወለጋ ዞኖች ጋር ድንበር እና ወሰኖችን ይጋራል።

 
በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን አካባቢ ግጭቶች የነበሩ ሲሆን የተከሰተው ግጭትም የብዙ ንፅሁንን ህይወት ቀጥፏል።  በዚህም ግጭት የተነሳ ከ30 ሺህ በላይ የሚሆኑ የአማራ እና የኦሮሞ ተወላጆች ከመኖሪያ ቦታቸው እንደተፈናቀሉ የሚያሳዩ መረጃዎች ወጥተው ነበር፡፡

በዚህ የፌስቡክ ገፅ ላይ የተሰራጨው ይህ መረጃም በዚህ ሀሳብ ላይ ተመስርቶ የተጋራ ነው።

የፌስቡክ ገፁ በቤንሻንጉል ክልል ካማሺ ዞን ውስጥ የኦሮሚያ ክልል ልዩ ሀይሎች ከኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ጋር በመሆን የአማራ ተወላጆችን ቤት እያቃጠሉ ነው የሚለውን መረጃ ይደግፍልኛል በማለት አንድ ምስልን አያይዞ ነበር።

ይሁን እንጂ ይህ የፌስቡክ ገጽ እንደተናገረው ምስሉ ከኦሮሚያ ክልል በመጡ ታጣቂዎች አማካኝነት የሚቃጠል የአማራ ተወላጆች ቤቶችን አያሳይም።

ሀቅቼክ የምስሉን ትክክለኛነት ለማጣራት ባደረገው ጥረት ምስሉን ታህሳስ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ላይ ከተጋራ አንድ ፅሁፍ ውስጥ አግኝቶታል። ይህ ምስል በቤንሻንጉል ክልል መተከል ዞን ውስጥ በነበረው ግጭት ላይ የተቃጠሉ ቤቶችን እንደሚያሳይ ከሚገልፅ ፅሁፍ ጋር አብሮ ተጋርቷል።

በዚህም ምክንያት ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ሀሰት፡ ምስሉ የመንግስት የፀጥታ ሀይሎች በአዲስ አበባ ከተማ በተማሪዎች ላይ ጥቃት ሲያደርሱ አያሳይም

በታህሳስ 5 ቀን 2015 ዓ.ም ላይ አንድ የፌስቡክ ገፅ “ወላጅ ልጆቹን ትምህርት እንዲቀስሙለት ትምህርት ቤት ይልካል ባለ ጊዜ እንዲህ ያደርጋል” የሚል ፅሁፍን በማያያዝ አንድ ምስልን አጋርቶ ነበር። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ400 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉ በቅርቡ በአዲስ አበባ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ከኦሮሚያ ክልል ባንዲራ ጋር ተነስቶ ከነበረው ግጭት ጋር የሚያያዝ እንዳልሆነ አረጋግጦ ምስሉን ሀሰት ብሎታል።  

ከሰሞኑ በአዲስ አበባ ውስጥ በሚገኙ አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ከኦሮሚያ ክልላዊ መዝሙር እና የባንዲራ መሰቀል ጋር ተያይዞ በተማሪዎች እና በፀጥታ አካላት መካከል ግጭት ተከስቶ እንደነበር የሚያሳዩ አንዳንድ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶች ሲዘዋወሩ ቆይተዋል።  

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ህዳር 28 ቀን 2015 ዓ.ም በይፋዊ የማህበራዊ ገፁ ላይ ባሰራጨው መረጃ መሰረት የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ከንቲባ አዳነች አቤቤ “በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እንዳይሰፍን የሚሰሩ የግጭት ነጋዴዎችን በጋራ በመከላከል አንድነታችንን ማጠናከር ይገባል እንዳሉ ያስነበበ ሲሆን ከንቲባዋ አያይዘውም ከሰሞኑ በአዲስ አበባ በሚገኙ አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ከሰንደቅ ዓላማ ጋር በማያያዝ ግጭት ለመቀስቀስ የተሞከረው ጥረት የዚሁ አካል መሆኑንም ገልፀዋል።” 

ህዳር 29 ቀን 2015 ዓም የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በከተማዋ ግጭትን ለመቀስቀስ እና ለማባባስ ሲሰሩ ነበሩ ያላቸውን 97 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልጿል።  

ፖሊስ በመግለጫውም ጨምሮ በቁጥጥር ስር የዋሉት ተማሪ እና አስተማሪዎች የኢትዮጵያ እና የኦሮሚያ ክልል ባንዲራን ከተሰቀለበት በማውረድ ግጭትን ለማባባስ ሲሰሩ የነበሩ መሆናቸውንም ጨምሮ ገልጿል። የአዲስ አበባ ከተማ የሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ሀላፊ የሆኑት ወ/ሮ ሊድያ ግርማ በታህሳሰ 3  ቀን 2015 ዓ.ም በሰጡት መግለጫ የፀጥታ ሀይሉ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ባሉ ትምህርት ቤቶች ወስጥ ግጭትን ለመቀስቀስ አስበዋል ያላቸውን 72 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልፀዋል።     

ከዚህ በተጨማሪም ሀቅቼክ በታህሰሳ 3 ቀን 2015 ዓ.ም በተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ አማራጮች ላይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የደንብ ልብስ የለበሱ የፀጥታ ሀይሎች በትምህርት ቤቶች አካባቢ ሲንቀሳቀሱ የሚያሳዩ ቪድዮውች ሲዘዋወሩ ተመልክቷል። 

በዚህ ሳምንት የወጡ አንዳንድ ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ የፌደራል መንግስት  በአዲስ አበባ በሚገኙ ትምህርት ቤቶች የኦሮምያ ክልል ባንዲራ እንዲሰቀልና መዝሙር እንዲዘመር እየተደረገ ያለው ግጭት ቀስቃሽ እንቅስቃሴ እንዲቆም መመሪያ መስጠቱን ያሳያሉ። 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም በነዚህ መረጃዎች ላይ ተመስርቶ የተጋራ ነው።

ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት ለማጣራት ባደረገው ጥረት ምስሉን በ2009 ዓ.ም የሂዩማን ራይትስ ዎች ድረገፅን ጨምሮ በሌሎች ድረገፆች ላይ በ2009 ዓ.ም በወቅቱ በነበረው የመንግስት ተቃውሞ  ላይ በኦሮሚያ ክልል ተፈጥሮ በነበረው አመፅ ምክንያት በኦሮሚያ የፀጥታ ሀይሎች የተያዙ ተማሪዎች ላይ ጥቃት ሲፈፅሙ የሚያሳይ እንደሆነ በሚያሳይ የፅሁፍ መግለጫ ስር ተጋርቶ አግኝቶታል። 

በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በተማሪዎች እና በፀጥታ አካላት መካከል ግጭት ተከስቶ እንደነበር የሚያሳዩ መረጃዎች ቢኖሩም ይህ የፌስቡክ ገፅ መረጃውን ይደግፍልኛል ብሎ ያጋራው ምስል የተሳሳተ ነው።በዚህም ምክንያት ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።  

ሀሰት፡ ይህ የሰው ልጅ ሲቃጠል የሚያሳየው ምስል ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈፀመ አይደለም

ከ39ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ህዳር 26 ፤ 2015 ዓ.ም ላይ “ይህ ፊልም አይደለም እዚሁ ሀገራችን ውስጥ ነው” የሚል ፅሁፍን በማያያዝ አንድ ምስልን አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ260 በላይ ግብረ-መልስን ሲያገኝ ከ60 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉ የቆየ እና በአሁኑ ሰዓት በኢትዮጵያ ውስጥ ካለው ወቅታዊ ሁኔታ ጋር የተያያዘ እንዳልሆነ በማረጋገጥ ምስሉን ሀሰት ብሎታል።

ምስሉ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጋራው ከ8 ዓመት በፊት መስከረም 26 ፤ 2007 ዓ.ም ላይ በአንድ የትዊተር አካውንት ላይ ነበር።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ኢትዮጵያ በተለያዩ የእርስ በርስ ግጭቶች እና አለመረጋጋቶች ውስጥ እያለፈች ትገኛለች። ውስጣዊ የድንበር ግጭቶች ፤ የብሄር ግጭት ፤ ሞት እና መፈናቀሎችም ተከስተዋል።

ከነዚህ ክስተቶች መሃልም በሰሜኑ የሀገሪቷ ክፍል በህወሓት እና በፌደራል መንግስት መካከል ተከስቶ የነበረው እና ለሁለት አመት ቆይቶ የነበረው የእርስ በርስ ጦርነት ይጠቀሳል።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በምዕራብ ኦሮሚያ ወለጋ ውስጥ በተከሰተው ግጭት ምክንያት በተደጋጋሚ የተለያዩ የጅምላ ግድያዎች ፤ ሞት እና መፈናቀሎች እየተሰሙ ይገኛሉ።

አዲስ ስታንዳርድ የተሰኘው የሀገር ውስጥ ጋዜጣ ህዳር 24 ፤ 2015 ዓ.ም ይዞ በወጣው ዘገባ መሰረት ህዳር 16 እና ህዳር 20 በምስራቅ ወለጋ ኪረሙ ዞን በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በአማራ ፋኖ እና ሚሊሽያ ታጣቂዎች አማካኝነት እንደተገደሉ የሚያሳይ አንድ የዜና ሪፖርት ይዞ ወጥቷል።

በዚህ የፌስቡክ ገፅ ላይ የተጋራው ይህ መረጃም በዚህ ሀሳብ ላይ ተመስርቶ የተጋራ ነው።

ስለዚህ ሀቅቼክ መረጃውን ለመደገፍ የተጋራውን ምስል መርምሮ ምስሉ ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈፀመ እንዳልሆነ አረጋግጧል።

ምስሉ ለመጀመሪያ ጊዜ የታተመው መስከረም 26 ፤ 2007 ዓ.ም በአንድ የትዊተር አካውንት ላይ ሲሆን “የህግ የበላይነት የታለ?” ከሚል የጥያቄ ፅሁፍ ጋር ተጋርቶ ነበር።

ይህን መረጃ ያጋራው የትዊተር አካውንት ከ30ሺህ በላይ ተከታይ ያለው ሲሆን አዳዲስ መረጃዎችን ከአፍሪካዊቷ ሀገር ማላዊ የሚያቀርብ እንደሆነ ይናገራል።

በዚህም ምክንያት ሀቅቼክ ይህ የፌስቡክ ገፅ መረጃውን ይደግፍልኛል ብሎ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ይህ ቪድዮ መንግስት ወታደሮቹን ከደብረዘይት አየር ሀይል ወደ አስመራ ሲያጓጉዝ ያሳያል?

ከ700ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ መስከረም 25 ቀን 2015 ዓ.ም “የአብይ መንግስት ወደ አስመራ ከደብረዘይት አየር ሀይል ግቢ በአንቶኖቭ ወታደሮችን ሲያመላልስ የሚያሳይ ቪድዮ ተመልከቱ። ስለ ሰላም እያወራን ወታደር ማሰማራት ትክክል አየደለም ለማንኛውም ሰራዊታችን TDF አይዘናጋም።” የሚል ፅሁፍ በማያያዝ አንድ የ25 ሰከንድ ርዝመት ያለው ቪድዮ አጋርቶ ነበር።”

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ11ሺህ በላይ እይታን ማግኘት ችሏል።
ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ቪድዮውን መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 


መስከረም 21 ቀን 2015 ዓ.ም የአፍሪካ ህብረት ሊቀ-መንበር ሙሳፋኪ ሀማት ለዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ደብዳቤ ጽፈው ነበር። ህብረቱ መስከረም 28 ፤ 2015 ዓ.ም ሊደረግ ታስቦ ወደነበረው የሰላም ድርድር በደብዳቤው ጋብዟቸዋል።  

መሰከረም 25 ፤ 2015 ዓ.ም ህወሓት ከአፍሪካ ህብረት የቀረበለትን የድርድር ጥያቄ መቀበሉን ባወጣው መግለጫ አሳውቋል። 

የኢትዮጵያ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በበኩሉ ባወጣው መግለጫ በአፍሪካ ህብረት ያቀረበውን የድርድር ጥያቄን እንደሚቀበለውና ከዚህ በፊትም የፌደራል መንግስት ግጭቱን ለማስቆም እና ሰላምን ለማውረድ የተቻለውን ሁሉ ሲያደርግ እንደቆየ ገልጿል።    

ሀቅቼክ በፌስቡክ ገፁ ላይ የተጋራውን ቪድዮ ለማጣራት ባደረገው ጥረት ነሀሴ 23 ፤ 2014 ዓ.ም የ4 ደቂቃ ከ5 ሴኮንድ ርዝመት ባለው ቪድዮ ውስጥ አግኝቶታል። ይህ ቪድዮም ከ9ሺህ በላይ ተከታይ ባለው የፌስቡክ ገፅ ላይ “የኢፌዴሪ የአየር ሀይል ልምምድን ተመልከቱ” በሚል የፅሁፍ መግለጫ ተጋርቶ ተገኝቷል። ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስም ቪድዮው ከ500 በላይ እይታን ማግኘት ችሏል።    

ከዚህ በተጨማሪ ሀቅቼክ በሁለቱ ቪድዮዎች ውስጥ ያሉ ተመሳሳይ ምስሎችን ለመመልከት ጥረት ያደረገ ሲሆን ከዚህ በታች የተመለከቱት ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው።     

ምስል አንድ

ምስል ሁለት 

በተጠቀሱት ምክንያቶች የተነሳ ቪድዮው የቆየ እና ይህ የፌስቡክ ገፅ ካጋራው መረጃ ጋር ፍጹም ያማይገናኝ እንደሆነ ሀቅቼክ አረጋግጧል። ስለዚህ ሀቅቼክ ቪድዮውን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ቪዲዮው ዳግም በተቀሰቀሰው ጦርነት የተማረኩ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን ያሳያል?

ከ 7 ሺ በላይ ተከታይ ያለው የትዊተር አካውንት መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም በስፋት ሲዘዋወር የነበረ አንድ ቪዲዮ አጋርቷል። ተንቀሳቃሽ ምስሉ ዳግም በተቀሰቀሰው ጦርነት ኢትዮጵያውያን የጦር እስረኞች ለሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ኃይሎች እጃቸውን ሲሰጡ እንደሚያሳይ በፅሁፍ መግለጫው ይናገራል።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ ቪዲዮ ከስድስት መቶ ጊዜ በላይ የተጋራ ሲሆን በትዊተር ላይ ብቻ ከ63 ሺህ በላይ ሰዎች ተመልክተውታል።

ይሁን እንጂ ቪዲዮው የቆየ እና በቅርቡ በቀጠለው ጦርነት በህወሓት ሃይሎች የተያዙ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን እንደማያሳይ ማረጋገጥ ተችሏል።

መጋቢት 15 ቀን 2014 ዓ.ም በኢትዮጵያ መንግስት እና በህወሓት ሃይሎች መካከል ለሰብአዊ እርዳታ የተኩስ አቁም ስምምነት ተደርጎ የነበረ ቢሆንም ነሀሴ 18 ቀን 2014 ዓ.ም በሁለቱ ሀይሎች መካከል ዳግም ግጭት አገርሽቷል።

ነሀሴ 10 ቀን 2014 ዓ.ም ሕወሓት በመጋቢት ወር መጨረሻ በጋራ የታወጀውን ጦርነት ማቆም ቀድሞ የፌደራል መንግስት እንደጣሰ በመግለጽ የፌደራል መንግስት ሃይሎች በመድፍና በታንክ በመታገዝ ጥቃት መሰንዘራቸውን ተናግሯል።

ሕወሃት በበኩሉ በአሁኑ ወቅት በህወሓት ሃይሎች ተይዘው ወደሚገኙ ግዛቶች ለመዝመት የሞከሩ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና የኤርትራ ጦር ክፍሎችን እንደደመሰሰ መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም ገልጿል።

ይህን ሁኔታ ታሳቢ በማድረግ የተማረኩ የጦር ምርኮኞችን እንደሚያሳይ በመግለጽ ቪዲዮው እንደገና በማህበራዊ ትስስር ገጾች ሊጋራ ችሏል።

ይህ ተንቀሳቃሽ ምስል ከዚህ ቀደም ግንቦት 11 ቀን 2014 ዓ.ም በአሜሪካ ድምጽ አማርኛ የፌስቡክ ገጽ ላይ “የትግራይ ክልል መንግሥት የጦር ምርኮኞች እንዲለቀቁ መወሰኑን አስታወቀ” በሚል ዜና ስር የተጋራ መሆኑን ሀቅቼክ አረጋግጧል። 

ስለሆነም ሀቅቼክ የትዊተር ፖስቱ መረጃውን እንዲደግፍለት የተጠቀመውን ቪዲዮ የቆየና ከተገለፀው ሁነት ጋር ተያያዥነት የሌለው በመሆኑ ሀሰት ብሎታል።

ቪድዮው በህወሓት አመራሮች ላይ የተፈፀመ የድሮን ጥቃትን ያሳያል?

ከሰሞኑ ፌስቡክ እና ዩቲዩብን ጨምሮ በተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ አውታሮች የተጋራ አንድ ቪድዮ “የፌደራል መንግስt ወታደራዊ ድሮኖችን በመጠቀም በህወሓት አመራሮች ላይ ጥቃት ሲፈፅም የሚያሳይ ቪድዮ” በሚል መግለጫ ሲዘዋወር ተስተውሏል።

ፌስቡክ ላይ ተጋርቶ የነበረው ቪድዮ ከግማሽ ሚልዮን በላይ ተመልካች ሲያገኝ በዩቲዩብ ላይ ተጋርቶ የነበረው ቪድዮ ከመቶ ሺህ በላይ እይታ ማግኘት ችሏል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ቪድዮው የፌደራል መንግስት ወታደራዊ ድሮኖችን ተጠቅሞ የህወሓት አመራሮችን ሲያጠቃ የሚያሳይ እንዳልሆነ አረጋግጧል። 

ጥቅምት 24 ፤ 2013 ዓ.ም በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል ግጭት ከተከሰተ በኋላ የፌደራል መንግስት ከሌሎች የክልል ልዩ ሀይል እና ሚሊሻዎች ጋር በመሆን ህወሓትን ከመቀሌ እና ከሌሎች የትግራይ ዋና ዋና ከተሞች ማስለቀቅ ችሎ ነበር።  

ይሁን እንጂ በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል የተከሰተው ይህ ጦርነት ህወሓት ከመቀሌ እና ከሌሎች ዋና ዋና የትግራይ ከተሞች ከለቀቀ በኋላ የሽምቅ ውጊያን መጠቀሙን ተከትሎ ጦርነቱ ሊራዘም ችሏል።

ይህን ተከትሎ የፌደራሉ መንግስት በጊዜው ተቋቁሞ ከነበረው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር በመሆን ግንቦት ወር 2013 ዓም ላይ የአንድ ወገን የተኩስ አቁም በማድረግ የመከላከያ ሰራዊቱን እና የክልል ልዩ ሀይል እና ሚሊሻዎችን ከትግራይ እና አካባቢው አስወጥቷል።

ይህን የፌደራሉ መንግስትን ውሳኔ ተከትሎ ህወሓት የክልሉን ዋና ከተማ መቀሌን መልሶ መቆጣጠር ችሎ ነበር። ከዚህ በመቀጠልም ህወሓት ጦሩን ወደ አማራ እና አፋር አጎራባች ክልሎች አንቀሳቅሷል። ይህን ተከትሎ የህወሓት ሀይሎችም የአማራ ክልል ትልልቅ ከተሞችን ጨምሮ ወደ አዲስ አበባ መቃረብ ችለው ነበር።    

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና ሌሎች ጥምር ሀይሎች በህወሓት ጦር ላይ የመልሶ ማጥቃት እርምጃን መውሰድ ከጀመሩ በኋላ የፌደራሉ መንግስት በህወሓት ሀይሎች ተይዘው የነበሩ የአፋር እና አማራ ክልል ቦታዎችን መልሶ መያዝ ችሏል። 

መጋቢት 15 ፤ 2014 ዓ.ም ላይ የፌደራሉ መንግስት ከህወሓት ጋር ያለውን ግጭት ለማቆም መወሰኑን ገልፆ ነበር። ህወሓትም በፌደራል መንግስት የተላለፈውን ይህን ውሳኔ እንደሚቀበል ገልፆ ነበር።

በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል የተፈጠረውን ግጭት ለማደራደር ከሶስተኛ ወግን ሀሳብ መቅረቡን ተከትሎ የሰላም እና የድርድር ጥረቶች ሲከናወኑ ቆይተዋል። ይህን ተከትሎም የቀድሞው የናይጄርያ ፕሬዝዳንት እና በአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል ሊደረግ የታሰበውን የድርድር እና የሰላም ውይይት እንዲያግዙ በአፍሪካ ህብረት ተሹመዋል።

ፕሬዝደንት ኦባሳንጆም የድርድር ሂደቱን ለማስጀመር በተደጋጋሚ በሁለቱ ወገኖች ጋር ተደጋጋሚ ውይይቶችን ሲያደርጉ ቆይተዋል።       

ነገር ግን ህወሓት በፕሬዝደንት ኦባሳንጆ የሰላም ድርድሩ ለመምራት መመረጣቸው ላይ እንደማያምንበት እና ከፊደራል መንግስቱ ጋር በሚደረገው የድርድር ሂደት ላይ ድርድሩን ለመምራት ብቁነታቸው ላይ ጥያቄ እንዳለው አስታውቋል። 

ህወሓት የፌደራል መንግስቱ ታንክ እና ከባድ መሳሪያዎችንም ተጠቅሞ ነሀሴ 10 ቀን 2014 ዓ.ም ጥቃት እንደሰነዘረበት ሕወሃት ገልፆ በመጋቢት ወር በሁለቱ ሀይሎች መካከል ተደርጎ የነበረውን ስምምነት የፈደራል መንግስት እንዳፈረሰው አስታውቋል።

በተጨማሪም ነሀሴ 18 ፤ 2014 ዓ.ም የፌደራል መንግስት በደቡባዊ የትግራይ አቅጣጫ ጥቃት እንደከፈተባቸው ህወሃት ገልጿል። 

ይሁን እንጂ የፌደራል መንግስት ይህ በህወሓት የቀረበው ውንጀላ ሀሰት መሆኑን በመናገር ህወሓት ወደ አጎራባች ክልልሎች ለመንቀሳቀስ የሚያረገውን ሙከራ ለማስቆም የትኛውንም ወታደርዊ እርምጃዎችን እንደሚወስድ አስታውቋል።   

የፊደራል መንግስት እየወሰደ ያለውን ወታደራዊ እርምጃ ተከትሎ በፌደራል መንግስት አማካኝነት እየተደረገ ያለ የድሮን ጥቃት በማለት የተለያዩ ተንቀሳቃሽ ምስሎች [ቪድዮውች] ሲዘዋወሩ ቆይተዋል። ይህ በፌስቡክና ዩቲዩብ ጨምሮ የተሰራጨው ቪድዮም ከነዚህ አንዱ ነው። 

ይሁን እንጂ ቪድዮው የፌደራል መንግስት በህወሓት አመራሮች ላይ ያደረሰውን የድሮን ጥቃት እንደማያሳይ ሀቅቼክ ማረጋገጥ ችሏል።    

በቪድዮው መሃል ያለው የቪድዮው ክፍል በፈረንጆቹ 2020 በአዘርባጃን እና በአርሜንያ መካከል የተከሰተውና ናጎርኖ ካራባህ እየተባለ በሚጠራው ጦርነት የቱርክ ድሮኖች የነበራቸውን እንቅስቃሴ የሚያሳይ ነው። 

ሀቅቼክ ቪድዮውን ለማግኘት ባደረገው ጥረት የቪድዮውን ክፍል መጋቢት 29 ፤ 2013 ዓ.ም በአንድ የዩቲዩብ ቻናል ላይ ተጋርቶ አግኝቶታል። 

በዚህም ምክንያትም ሀቅቼክ በፌስቡክ እና በዩቲዩብ ላይ ሲዘዋወር የነበረው ቪድዮ ሀሰት መሆኑን አረጋግጧል። 

ሀሰት ፡ ምስሉ በራያ ግንባር የተማረኩ የጦር መሳሪያዎችን አያሳይም

ከ120 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ነሀሴ 28 ፤  2014 ዓ.ም ላይ “በራያ ግንባር ከጠላት የተማረከ 430 ክላሽንኮቭ እና 3 ዲሽቃ ፤ ጠላት የጥምር ጦሩ ብርቱ ክንድ መቋቋም ያልቻለው ሀይል እየተማረከ ነው” የሚል ፅሁፍ በማያያዝ አንድ ምስልን አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ ፅሁፍ ከአንድ ሺህ በላይ ግብረመልስ ሲያገኝ ከ150 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።  

ጥቅምት 24 ፤ 2013 ዓ.ም በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል ግጭት ከተከሰተ በኋላ የፌደራል መንግስት ከሌሎች የክልል ልዩ ሀይል እና ሚሊሻዎች ጋር በመሆን ህወሓትን ከመቀሌ እና ከሌሎች የትግራይ ዋና ዋና ከተሞች ማስለቀቅ ችሎ ነበር።  

ይሁን እንጂ በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል የተከሰተው ይህ ጦርነት ህወሓት ከመቀሌ እና ከሌሎች ዋና ዋና የትግራይ ከተሞች ከለቀቀ በኋላ የሽምቅ ውጊያን መጠቀሙን ተከትሎ ጦርነቱ ሊራዘም ችሏል።

ይህን ተከትሎ የፌደራሉ መንግስት በጊዜው ተቋቁሞ ከነበረው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር በመሆን ግንቦት ወር 2013 ዓም ላይ የአንድ ወገን የተኩስ አቁም በማድረግ የመከላከያ ሰራዊቱን እና የክልል ልዩ ሀይል እና ሚሊሻዎችን ከትግራይ እና አካባቢው አስወጥቷል።

ይህን የፌደራሉ መንግስትን ውሳኔ ተከትሎ ህወሓት የክልሉን ዋና ከተማ መቀሌን መልሶ መቆጣጠር ችሎ ነበር። ከዚህ በመቀጠልም ህወሓት ጦሩን ወደ አማራ እና አፋር አጎራባች ክልሎች አንቀሳቅሷል። ይህን ተከትሎ የህወሓት ሀይሎችም የአማራ ክልል ትልልቅ ከተሞችን ጨምሮ ወደ አዲስ አበባ መቃረብ ችለው ነበር።    

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና ሌሎች ጥምር ሀይሎች በህወሓት ጦር ላይ የመልሶ ማጥቃት እርምጃን መውሰድ ከጀመሩ በኋላ የፌደራሉ መንግስት በህወሓት ሀይሎች ተይዘው የነበሩ የአፋር እና አማራ ክልል ቦታዎችን መልሶ መያዝ ችሏል። 

መጋቢት 15 ፤ 2014 ዓ.ም ላይ የፌደራሉ መንግስት ከህወሓት ጋር ያለውን ግጭት ለማቆም መወሰኑን ገልፆ ነበር። ህወሓትም በፌደራል መንግስት የተላለፈውን ይህን ውሳኔ እንደሚቀበል ገልፆ ነበር።

በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል የተፈጠረውን ግጭት ለማደራደር ከሶስተኛ ወግን ሀሳብ መቅረቡን ተከትሎ የሰላም እና የድርድር ጥረቶች ሲከናወኑ ቆይተዋል። ይህን ተከትሎም የቀድሞው የናይጄርያ ፕሬዝዳንት እና በአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ የሆኑት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል ሊደረግ የታሰበውን የድርድር እና የሰላም ውይይት እንዲያግዙ በአፍሪካ ህብረት ተሹመዋል።

ፕሬዝደንት ኦባሳንጆም የድርድር ሂደቱን ለማስጀመር በተደጋጋሚ በሁለቱ ወገኖች ጋር ተደጋጋሚ ውይይቶችን ሲያደርጉ ቆይተዋል።       

ነገር ግን ህወሓት በፕሬዝደንት ኦባሳንጆ የሰላም ድርድሩ ለመምራት መመረጣቸው ላይ እንደማያምንበት እና ከፊደራል መንግስቱ ጋር በሚደረገው የድርድር ሂደት ላይ ድርድሩን ለመምራት ብቁነታቸው ላይ ጥያቄ እንዳለው አስታውቋል። 

ህወሓት የፌደራል መንግስቱ ታንክ እና ከባድ መሳሪያዎችንም ተጠቅሞ ነሀሴ 10 ቀን 2014 ዓ.ም ጥቃት እንደሰነዘረበት ሕወሃት ገልፆ በመጋቢት ወር በሁለቱ ሀይሎች መካከል ተደርጎ የነበረውን ስምምነት የፈደራል መንግስት እንዳፈረሰው አስታውቋል።

በተጨማሪም ነሀሴ 18 ፤ 2014 ዓ.ም የፌደራል መንግስት በደቡባዊ የትግራይ አቅጣጫ ጥቃት እንደከፈተባቸው ህወሃት ገልጿል። 

ይሁን እንጂ የፌደራል መንግስት ይህ በህወሓት የቀረበው ውንጀላ ሀሰት መሆኑን በመናገር ህወሓት ወደ አጎራባች ክልልሎች ለመንቀሳቀስ የሚያረገውን ሙከራ ለማስቆም የትኛውንም ወታደራዊ እርምጃዎችን እንደሚወስድ አስታውቋል።   

ነሀሴ 23 ቀን 2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በተለያዩ የጦር ግንባሮች ድል እያስመዘገበ እንደሆነ ተናግሯል።

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህን ሁኔታ መሰረት አድርጎ ተጋርቷል። 

ሀቅቼክ ምስሎቹን ትክክለኛነት ለማጣራት ባደረገው ጥረት ምስሎቹን በአማራ ሚድያ ኮርፖሬሽን የዩቲዩብ ቻናል ላይ ጥር 25 ፤ 2014 ዓ.ም በቀረበ የዜና ቪድዮ ላይ አግኝቷቸዋል። ይህ ጽሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የዩቲዩብ ቪድዮው ከ150ሺህ ጊዜ በላይ ታይቷል። 

የመጀመርያው ምስል በዜና ቪድዮው በ23ተኛ ደቂቃ ከ05 ሴኮንድ ላይ ይገኛል  

ሁለተኛው ምስል በዜና ቪድዮው በ22ተኛ ደቂቃ ከ57ተኛ ሴኮንድ ላይ ይገኛል

የዜና ቪድዮው፣ “በመከላከያ ሰራዊት እና በፌደራል ፖሊስ ጥምር ሃይል አማካኝነት በአሸባሪው ኦነግ ሸኔ ላይ በተወሰደው ርምጃ ከ100 በላይ የሚሆኑ አባላቱ ተደምስሰዋል” በሚል ርዕስ የቀረበ ሲሆን በተጨማሪም በቪድዮው ተማረኩ ያላቸውን የሽብር ቡድኑን አባሎች ያሳያል። በዚህም መሰረት መረጃውን ለመደገፍ ከፖስቱ ጋር የተያያዙትን ምስሎች ሀቅቼክ ሀሰት ብሏቸዋል።

ምስሉ በአላማጣ አካባቢ በተፈፀመ የአየር ጥቃት የወደሙ ታንኮችን ያሳያል?

ከ130ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ መስከረም 4፤ 2015 ዓ.ም ላይ “አላማጣ ኳስ ሜዳ ተብሎ በሚጠራ ስፍራ በተፈፀመ የአየር ጥቃት ወደ ቆቦ እየተጫኑ የነበሩ ሁለት ታንኮች መመታታቸው ታውቋል” የሚል ፅሁፍን በማያያዝ አንድ ምስልን አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ800 በላይ ግብረመልስ ሲያገኝ ከ30 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል።    

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 

ጥቅምት 24 ፤ 2013 ዓ.ም በህወሓት እና በፌደራል መንግስቱ መካከል የተከሰተው ግጭት ከአንድ ዓመት በላይ አሳልፏል። 

በሰኔ ወር 2013 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ የፌደራል መንግስት ከትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በቀረበለት ጥያቄ መሰረት የአንድ ወገን የተኩስ አቁም ስምምነትን በማድረግ የመከላከያ እና የክልል ልዩ ሃይሎችን ከትግራይ ክልል አስወትቷል። 

ይህን ተከትሎ ለዘጠኝ ወራት ቆይቶ የነበረው የተኩስ አቁም ስምምነት [ለሰብዓዊ እርዳታ] ነሀሴ 18 ፤ 2014 ዓ.ም  ዳግም ወደ ግጭት ገብቷል።    

መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም በድምፂ ወያኔ ስም የተከፈተ እና ከ600ሺህ ተከታይ ባለው የፌስቡክ ገፅ ላይ በቀረበ ሪፖርት የፌደራሉ መንግስት በድምፂ ወያኔ የቴሌቪዥን ጣብያ ላይ የድሮን ጥቃት ማድረሱን ተገልጿል።  

መስከረም 14 ፤ 2015 ዓ.ም የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል እና ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ በይፋዊ የትዊተር ገፃቸው ላይ “የፌደራሉ መንግስት ከደቂቃዎች በፊት በመቀሌ ከተማ ላይ የድሮን ጥቃት አድርሷል።” የሚል ፅሁፍን አጋርተው ነበር።

ሀቅቼክ ምስሉን ለማጣራት ባደረገው ጥረት ምስሉን የካቲት 27 ፤ 2014 ዓ.ም ጽሁፎችን በዩክሬን ቋንቋ በሚያቀርብ suspline.media በተሰኘ አንድ ድረገፅ ላይ አግኝቶታል። 

ምስሉን “የትራንስካርፓቲያን ብርጌድ ተዋጊዎች የሩሲያን BMP ታንክ ሲያወድሙ አንድ ወታደር መማረክ ችለዋል” በሚል  ፅሁፍ ስር ሀቅቼክ ያገኘው ሲሆን በፅሁፉም ውስጥ የወደሙ የሩስያ BMP ታንኮች እና የተማረከ የሩሲያ ወታደር ምስል ተካተዋል።

በ2014 እ.አ.አ በሩሲያ እና በዩክሬን መካከል በተከሰተው ግጭት በየካቲት 17 ቀን 2014 ዓ.ም ሩሲያ ዩክሬንን ወራለች። በሩሲያ የተጀመረው ወረራ ከሁለተኛው የአለም ጦርነት በኋላ በአውሮፓ ውስጥ ትልቁን የስደተኞች ቁጥር እንዲመዘገብ ምክንያት ሆኗል። በዚህም ምክንያት ወደ 7.3 ሚሊዮን(አንድ ሶስተኛ) የሚሆኑ ዩክሬናውያን ለስደት ተዳርገዋል።

ሊንክ

የፌደራል መንግስት በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል እየተደረገ ባለው ጦርነት የተለያዩ የአየር ጥቃቶችን እያደረገ እንደሆነ የሚያሳዩ የተለያዩ መረጃዎች ቢኖሩም በፌስቡክ ገፁ መረጃውን ይደግፍልኛል በማለት የተጠቀመው ምስል የተሳሳተ ነው።
ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገጹ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

Exit mobile version