የተጣሩ መረጃዎች

ምስሉ በቅርቡ ቦሌ አራብሳ አካባቢ ሁለት ህፃናትን የገደለችው ግለሰብ ያሳያል?

አንድ ከ200 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ነሀሴ 27 ፤ 2014 ዓ.ም ላይ “ሁለቱን እንቦቀቅላ ህፃናትን በጭካኔ አርዳ እና አንቃ የገደለችው ግለሰብ እቺ ናት” የሚል ፅሁፍን በማያያዝ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ9 ሺህ በላይ ግብረመልስን ሲያገኝ ከ1400 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱን መርምሮ ምስሉን ሀሰት ብሎታል።    

ነሀሴ 26 ፤ 2014 ዓ.ም በተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ አውታሮች ላይ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ አራብሳ ኮንዶሚንየም ተብሎ በሚጠራው የጋራ መኖሪያ ቤት መንደር አካባቢ በቤት ሰራተኛ አማካኝነት የ2 እና 3 አመት ህፃናት እንደተገደሉ ተነግሮ ነበር።

ነሀሴ 26 ፤ 2014 ዓ.ም ቢቢሲ አማርኛ ያናገራቸው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ምክትል ኮማንደር ማርቆስ ታደሰ “እጅግ በጣም አሳዛኝ እና ዘግናኝ” በተባለው በዚህ ወንጀል የተጠረጠረችው የቤት ሠራተኛ የ19 ዓመት ወጣት መሆኗን የገለፁ ሲሆን በሁለት ህጻናት ላይ ግድያው ከተፈጸመች በኋላ ተጠርጣሪዋ ወንጀሉን መፈጸሟን በማመን ለፖሊስ እጇን ከሰጠች በኋላ በቁጥጥር ስር መዋሏን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

 ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህንን መረጃ መሰረት አድርጎ ተጋርቷል። 

ነገርግን ሀቅቼክ የጎግል የተገላቢጦሽ ምስል ፍለጋን ተጠቅሞ ምስሉን ለማጣራት ባደረገው ጥረት ምስሉን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት ከሀገር ተሰደው የነበሩ ፖለቲከኞችን ወደ ሀገር እንዲመለሱ መጋበዛቸውን ተከትሎ ሐምሌ 29 ቀን 2010 ዓ.ም አክቲቪስት እና ፖሊቲከኛ ጀዋር መሀመድን ለመቀበል በተደረገ ስነ ስርዓት ላይ ቦምብ ለመጣል የተዘጋጀች ግለሰብ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሏን ከሚገልጽ ፅሁፍ ጋር ተጋርቶ አግኝቶታል። 

ሊንክ

ከሰሞኑን በቦሌ አራብሳ ኮንዶሚኒየም አካባቢ በሰራተኛቸው አማካኝነት የተገደሉ ህፃናት ቢኖሩም ይህ የፌስቡክ ገፅ የሰራተኛዋን ምስል ያሳያል ብሎ የተጠቀመው ምስል የተሳሳተ ነው።
ስለዚህም ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 

የሃሰተኛ ዜና ጥቆማ፡ ዮናስ ዘውዴ ወደ ሌላ የስራ መደብ ተዘዋወረ እንጂ በራሱ ፈቃድ ከኃላፊነቱ አልለቀቀም

በአንድ የፌስቡክ ፖስት ሀምሌ 7 ቀን የተላለፈ መረጃ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሀላፊ አቶ ዮናስ ዘውዴ ከስራው በገዛ ፈቃዱ መልቀቁን አስታውቆ ነበር። ይህ ፖስት ዮናስ ዘውዴ ራሱ እንደተናገረው በመጥቀስ “አሁን ያለው አገዛዝ በሙስና የተዘፈቀ እና ለሀገሪቱ መፃኢ ዕድል የማያስብ ስለሆነ አብሬ ልቀጥል ባላመቻሌ በራሴ ፍቃድ ከሃላፊነቴ ለቅቄያለው” ማለቱን ፅፏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የቀድሞ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሙኒኬሽን ቢሮ ሀላፊ አቶ ዮናስ ዘውዴ ከኃላፊነቱ አለመልቀቁንና በመስተዳድሩ ወደ ሌላ የስራ መደብ መዘዋወሩን አረጋግጧል።    

አቶ ዮናስ ዘውዴ ከኃላፊነቱ በገዛ ፈቃዱ ለቋል የሚለው የዚህ የፌስቡክ ፖስት መረጃ የተሰራጨው የተለያዩ የመንግስት ባላስልጣናት ከኃላፊነታቸው በተነሱበትና በቁጥጥር ስር በዋሉበት ሰሞን ነው።  

ባለፈው ሳምንት የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር የሆኑት አቶ ምትኩ ካሳ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው የፌደራል ፖሊስ በቁጥጥር ስር ውለዋል። 

የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር በቅርቡ ለዕድለኞች የወጣውን የኮንዶሚኒየም ዕጣ በአስተዳደሩ ውስጥ የሚሰሩ ሰራተኞች እና አንዳንድ ባለስልጣናት በዕጣው የማጭበርበር ሂደት ውስጥ ተሳትፈዋል በማለት የእጣ አወጣጥ ሂደቱ እንደሚደገም አስታውቋል። በማጭበርበር ሂደቱም ላይ ተሳትፈዋል ያላቸውን ግለሰቦች ላይ የምርመራ መዝገብ ተከፍቶባቸዋል።

የቀድሞው የአዲስ አበባ መስተዳድር የኮሙኒኬሽን ሃላፊ ከስራ የመልቀቅ መረጃዎች መሰማት የጀመሩትም የኮንዶሚኒየም የዕጣ አወጣጥ ውዝግብ ባስነሳበት ወቅት ላይ ነበር።           

አቶ ዮናስ ዘውዴ የብልፅግና ፓርቲ አባል ሲሆን በስድስተኛው ሃገር አቀፍ አጠቃላይ ምርጫ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አባል ሆኖ ተመርጧል። ይህንንም ተከትሎ በከተማዋ ከንቲባ አማካኝነት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ተደርጎ ተሹሟል።  

የአቶ ዮናስ ከኃላፊነት የመልቀቅ መረጃን ተከትሎ አል-አይን አማርኛ ባቀረበው ሪፖርት የቀድሞው የኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ወደ ሌላ የስራ መደብ መዘዋወሩን ገልጿል። በሪፖርቱም በዶ/ር ዮናስ ምትክ በቦታው የተሾሙት አቶ አብዲ ፀጋዬ የአቶ ዮናስን ወደ ሌላ የስራ መደብ መዘዋወሩን አረጋግጠዋል። 

ሃቅ ቼክ በጉዳዩ ዙሪያ መልስ ለማግኘት አቶ ዮናስ ዘውዴን በስልክ ያገኘው ሲሆን በጉዳዩ ላይ አስተያየት መስጠት እንደማይፈልግ ገልጾ ስለ ጉዳዩ ያለውን ትክክለኛ መረጃ ራሱ ይፋ እንደሚያደርግ ተናግሯል።    

በዚህም መሰረት የቀድሞ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ የነበረው አቶ ዮናስ ዘውዴ በገዛ ፈቃዱ ከኃላፊነቱ አለመልቀቁን እንዲሁም ወደሌላ የስራ መደብ እንደተዘዋወረ ሃቅ ቼክ አረጋግጧል።  

ህወሓት አውሮፕላን አግቷል?

አንድ በዩቲዩብ የተሰራጨ ቪድዮ በፊት ገፁ ላይ “ህወሓት አውሮፕላን አገተ” በሚል ርዕስ ሰኔ 16 ቀን 2014 ዓ.ም መረጃ አጋርቶ ነበር። ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ ቪድዮ ከ2500 በላይ እይታ ማግኘት ችሏል።

ሀቅቼክ ሙሉ ቪድዮውን በመመልከት ቪድዮው በውስጡ ህወሓት አውሮፕላን እንዳገተ የሚገልፅ ምንም አይነት መረጃ እንደሌለው የተገነዘበ ሲሆን በአንፃሩ ህወሓት አውሮፕላን መቀሌ እንዳያርፍ መከልከሉን ይናገራል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ በዚህ የዩቲዩብ ቪድዮ የተላለፈውን መረጃ አሳሳች ብሎታል።  

ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም በህወሓት እና በፌደራል መንግስት መካከል የተጀመረው ጦርነት እስካሁን ድረስ ማብቂያ አላገኘም።   

ከመጋቢት ወር 2014 ዓ.ም ጀምሮ በሁለቱ ተዋጊ ሀይሎች መካከል ለሰባዊ እርዳታ በሚል በተፈጠረው የተኩስ አቁም ስምምነት የሰብዓዊ እርዳታ ፍሰቱን እንዳሻሻለው ተነግሯል።    

ይህ በእንዲህ እንዳለ በህወሓት አመራሮች እና በፌደራል መንግስት መካከል ቀጥተኛ ውይይቶች እንደነበሩ የሚዘግቡ ያለተረጋገጡ ሪፖርቶች ሲወጡ ቆይተዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፌደራል መንግስት ከህወሓት ጋር ድርድር እና ውይይት ለማድረግ እንደተቃረቡ የሚያሳዩ አንዳንድ መረጃዎች እየተሰሙ ነው። 

የህወሓት አመራር የሆኑት ደብረፅዮን ገብረሚካኤል በፃፉት ግልፅ ደብዳቤ አማካኝነት አስተዳደራቸው ሰላም ለማውረድ ለሚደረገው ድርድር ተወካዮቻቸውን ወደ ናይሮቢ ኬንያ እንደሚልኩ ገልፀዋል።   

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለሚቀርቡላቸው ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት በተገኙበት መድረክ የፌደራሉ መንግስት ከህወሓት ጋር ለሚደረግው ድርድር ኮሚቴ ማዋቀሩን ገልፀዋል። 

በሌላ መልኩ በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል የሰብዓዊ እርዳታ እና መጓጓዣ መንገዶችን አስመልክቶ ይሚነሱ አንዳንድ ውዝግቦች ተስተውለዋል። በዚህም የፌደራል መንግስት እና ህወሓት የሰብዓዊ እርዳታ ተደራሽነትን ማደናቀፍን አስመልክቶ እስር በእርስ ሲካሰሱ ቆይተዋል። 

ባለፈው መሰከረም ወር የአለም የምግብ ፕሮግራም (WFP) ወደ ትግራይ ከገቡት 445 የዕርዳታ መኪናዎች ውስጥ 407 የሚሆኑት መመለስ አንዳልቻሉ ገልጿል። በተመሳሳይ ሁኔታም ሰኔ 16 ፤ 2014 ዓ.ም ወደ ትግራይ ሲጓዙ የነበሩ የዕርዳታ አውሮፕላኖች መቀሌ አየር ማረፍያ እንዳይወርዱ አግዷል በማለት የፌደራል መንግስት ህወሓትን ከሷል። ህወሓት ለፌደራል መንግስት ክስ አየር መንገዱ በነዳጅ እጥረት ምክንያት መስራት ማቆሙን በመግለፅ ምላሽ ሰጥቷል። 

የዩቲዩብ ቪድዮው የተጠቀሱትን ነባራዊ ሁኔታዎች ተገን በማድረግ እንደተጋራ መረዳት ይቻላል። ይህ የዩቲዩብ ቪድዮ “ህወሓት አውሮፕላን አገተ” በሚል ርዕስ ቪድዮውን ያጋራ ቢሆንም በቪድዪው የሚተላለፈው መልዕክት ህወሓት ወደ መቀሌ የሚደረጉትን በረራዎች በመከልከል የሰብዓዊ እርዳታ ተደራሽነትን ማስተጓጎሉን ይገልፃል። ይህም በፊት ገፁ ላይ ያለው ርዕስ እና በውስጥ ያለው መረጃ የማይገናኝ መሆኑን ያሳየናል።  ከነዚህ ምክንያቶች በተነሳ ሀቅቼክ ቪድዮውን መርምሮ አሳሳች ብሎታል። 

ቪድዮው በምዕራብ ወለጋ የተደረገውን ግድያ ያሳያል?

ከ196ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ በሰኔ 14 ቀን 2014 ዓ.ም ያሰራጨውን ቪድዮ “የምዕራብ ወለጋው ጭፍጨፋ በጥቂቱ ማሳያ ምስል..” የሚል ፅሁፍ በማያያዝ አጋርቶ ነበር። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ቪድዮው ከ140ሺህ በላይ እይታ ሲያገኝ ከ3500 በላይ ግብረ መልስ አግኝቷል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ቪድዮውን አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።  

ሰኔ 7 ፤ 2014 ዓ.ም በጋምቤላ ዋና ከተማ የኦነግ ሸኔ እና የጋምቤላ ነፃ አውጪ ግምባር ጥምር ሀይሎች ከከተማዋ ከመንግስት ሀይሎች ጋር የተኩስ ልውውጥ አድርገው እንደነበር ተዘግቧል። እንደ ዘገባዎቹ ሁለቱ አማፅያን ሀይሎች በድንገት ከተማዋን በመቆጣጠር በመንግስት ሀይሎች ላይ ተኩስ ከፍተዋል። 

ነገር ግን ብዙም ሳይቆይ መንግስት ሁኔታውን በቁጥጥር ስር እንዳዋለው ገልጿል።

በተመሳሳይ ቀን እና በተቀራራቢ ጊዜ በደምቢ ዶሎ እና በምዕራብ ወለጋ ጊምቢ ከተማዎች በኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች እና በመንግስት ሀይሎች መካከል ግጭት ተፈጥሮ እንደነበርና በአንዳንድ ሪፖርቶች መሰረትም የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ከተሞቹን በቁጥጥራቸው ስር ማዋላቸውን ገልጸው ነበር።  

ሰኔ 11 ፤ 2014 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢ ወረዳ ቶሌ ቀበሌ የአማራ ብሔር ተወላጆች በሚኖሩባቸው መንደሮች በተፈጸመው ጥቃት በመቶዎቹ የሚቆጠሩ ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውንና ሺዎች ደግሞ አካባቢውን ለቀው መውጣታቸውን ነዋሪዎችን እማኝ ያደረጉ ዜናዎች በሰፊው ተሰራጭተዋል።

ሆኖም የኦነግ ሸኔ አለማቀፍ ቃል አቀባይ የሆነው ኦዳ ተርቢ በትዊተር አካውንቱ ዘገባውን አስተባብሏል።       

ኦነግ ሸኔ መረጃዎችን ይፋ በሚያደርግበት የኮምዩኒኬ ድረ-ገፁ ላይ መንግስት ያደራጃቸው “ጋቸና ሲርና” የሚል ስም የተሰጣቸው የሚሊሽያ ቡድኖች እንዳሉና እነሱም የኦነግ ሸኔ አባሎችን ለመምሰል አርቴፊሻል ዊግ እና ሹሩባዎችን እንደሚያደርጉ ተገልጿል።

ሀቅቼክ ቪድዮውን ለማጣራት ባደረገው ጥረት ቪድዮው ከዚህ በፊት ሐምሌ 16 ፤ 2013 ዓ.ም በአንድ የፌስቡክ አካውንት “የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት የፖለቲካ እስረኞችን ያለምንም ፍርድ እየተሰቃዩ የነበሩትን በማስፈታት ነጻ አውጥቷል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ጉዞ ወደ 4ኪሎ በሚል መርህ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ የሰራዊቱ ኮማንዶዎች በመገስገስ ላይ ይገኛሉ” በሚል ጽሁፍ ተጋርቶ ነበር። ይህ ቪድዮም ከ460 በላይ እይታን ማግኘት ችሏል። 

ሀቅቼክ በሁለቱ ቪድዮዎች ውስጥ ተመሳሳይ ሲቪል ሰዎችን እና ታጣቂዎችን መመልከት ችሏል።

በምዕራብ ወለጋ የተፈፀሙ የተለያዩ ዘርን መሰረት ያደረጉ ጭፍጨፋዎች እንደተፈፀሙ ሪፖርቶች ቢወጡም ይህ የፌስቡክ ገፅ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመው ቪድዮ የቆየ መሆኑን ማወቅ ተችሏል።
ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱን መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 

ህወሓት ከፌደራል መንግስት ጋር ድርድር እንደማይፈልግ አስታውቋል?

አንድ የዩቲዩብ ቻናል በግንቦት ወር 2014 ዓ.ም ህወሓት ከኢትዮጵያ የፌደራል መንግስት ጋር ድርድር እንደማይፈልግ ገለፀ በሚል ርዕስ አንድ ቪድዮ አጋርቶ ነበር።

ሆኖም ቪድዮው ሲጫወት ያለው መልዕክት ህወሓት ያስቀመጣቸው አምስት የቅድመ ድርድር ነጥቦች እንዳሉ ይናገራል። የቪድዮው ርዕስ እና የሽፋን ምስል ህወሓት ድርድር እንደማይፈልግ የሚያስቀምጥ ቢሆንም የቪድዮው ይዘት ግን ህወሓት ለድርድሩ ያስቀመጣቸውን አምስት ቅድመ ሁኔታዎች ይናገራል። 

በዚህም ምክንያት ሀቅቼክ የዩቲዩብ ቪድዮው ያስተላለፈውን መልዕክት መርምሮ አሳሳች ብሎታል።

የፌደራል መንግስት እና ህወሓት እስካሁን ድረስ መፍትሄ ባላገኘ ጦርነት ውስጥ ይገኛሉ። 

በመጋቢት ወር 2014 ዓ.ም ሁለቱ ተዋጊ ሀይሎች የተኩስ አቁም ስምምነት [ለሰብዓዊ እርዳታ] ማድረጋቸው የሚታወስ ሲሆን ከዚያን በኋላ የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦቱ እየተሻሻለ መቷል።   

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፌደራል መንግስቱ እና በህወሓት ከፍተኛ አመራሮች መካከል ቀጥተኛ ንግግሮች እንደተደረጉ የሚያሳዩ ያልተረጋገጡ ሪፖርቶች ሲወጡ ቆይተዋል።

ይህ በእንዲህ እያለ የፌደራል መንግስቱ ከህወሓት ጋር ድርድሮችን ሊያደርግ እንደሆነ የሚያሳዩ የተለያዩ መረጃዎች እየወጡ ይገኛሉ።

ባለፈው ሳምንት ለ ሞንድ የተባለ የፈረንሳይ ጋዜጣ በድረ-ገጹ የኢትዮጵያ የፌደራል መንግስት ከህወሓት ጋር በግንቦት ወር መጨረሻ አካባቢ በታንዛኒያ አሩሻ ድርድር ሊያደርጉ እቅድ እንደተያዘ የሚገልፅ ፅሁፍ አስነብቧል። 

ይህ የፈረንሳይ ጋዜጣ ከተለያዩ የዲፕሎማት ምንጮቼ አግኝቼዋለው ባለው መረጃ መሰረት ህወሓት በምዕራብ ትግራይ ድንበር አካባቢ ላይ ያሉ ቦታዎች ላይ የሚያነሳውን የባለቤትነት ጥያቄ ትቶታል ብሎ ዘግቧል።   

ሆኖም ህወሓት ውዝግብ የተፈጠረባቸው የምዕራብ ትግራይ ቦታዎች ላይ ያለውን ጥያቄ ትቶታል የሚለው መረጃ ውሸት እንደሆነ አስታውቋል። 

ይህን ተከትሎ የህወሓት ሊቀመንበር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ለተለያዩ አካላት በፃፉት ግልፅ ደብዳቤ የሰላም ድርድር ለማድረግ ወደ ኬንያ ናይሮቢ የትግራይ ተወካዮችን እንደሚልኩ አስታውቋል። በአንፃሩ ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከፓርላማ ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሲሰጡ የፌደራሉ መንግስት ከህወሓት ጋር ለመደራደር ኮሚቴ እንዳዘጋጀም ተናግረዋል። 

በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድም ሆኑ ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ምስጢራዊ ውይይትም ሆነ ድርድር እንዳልተደረገ ገልፀዋል። 

ህወሓት በቅርብ በሰጠው መግለጫ በድርድሩ እንዲጠበቁለት የሚፈልጋቸውን ቅድመ ሁኔታዎች አስቀምጧል። ከነዚህም መካከል የምዕራብ ትግራይ ቦታዎች ጉዳይ፣ የሪፈረንደም ህዝበ ውሳኔ፣ የጦር ኃይሉን ይዞ መቀጠል እና በትግራይ ለተፈጠረው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተጠያቂነት የሚሉትን አስቀምጧል።

ሰኔ 9 ቀን 2014 ዓ.ም የህወሓት አመራር የሆኑት ፕሮፌሰር ክንደያ ገብረህይወት በትዊተር አካውንታቸው ህወሓት አልደራደርባቸውም የሚላቸውን አምስት ነጥቦች አስፍረዋል።         

ቪድዮው ይህን ሁኔታ ተገን በማድረግ የተለቀቀ ሲሆን በዚድዮው የተላለፈው መልዕክት ይዘት ህወሓት ለድርድር ስላስቀመጣቸው አምስት ነጥቦች ሆኖ ሳለ በቪድዮው ሽፋንና ርዕስ የተቀመጠው ምስልና ህወሓት ድርድር እንደማይፈልግ የሚገልፀው ርዕስ አሳሳች ያደርገዋል። 

በተጨማሪም ሀቅቼክ ህወሓት ከፌደራል መንግስት ጋር ለመደራደር የቅድመ ድርድር ነጥቦቹን እንዳስቀመጠ እንጂ ድርድር እንደማይፈልግ እንዳልገለፀ አጣርቷል። ስለዚህ ሀቅቼክ በዩቲዩብ ቪድዮው ሽፋኑ እና ርዕስ እንዲሁም በውስጥ ይዘቱ መልዕክት መካከል ያለውን ግንኙነት አጣርቶ አሳሳች ብሎታል።

የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ናቸው?

ሰኔ 2  ቀን 2014 ዓ.ም በአንድ የዩቲዩብ ቻናል ላይ የተላለፈ ቪድዮ ባሰራጨው መልዕክት የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እንደሆኑ ጠቅሶ ነበር። ቪድዮውም በመቀጠል ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ጋር ያላት ግንኙነት እየጠነከረ እንደመጣ ገልጾ በተቃራኒው ደግሞ ኤርትራ ከአሜሪካ ጋር ያላት ግንኙነት ደግሞ ይበልጥ እየሻከረ እንደመጣ ይናገራል።

ቪድዮው በትንታኔው በኤርትራው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና በአስመራ የአሜሪካ ኤምባሲ መካከል በፖለቲካ ፤ በሃይማኖት እና በአለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ አለመስማማት እና ጭቅጭቆች እንዳሉ በመናገር ይህም ለሁለቱ ሀገሮች ግንኙነት መሳሳት ይበልጥ አስተዋጽኦ እንዳደረገ ይናገራል።

አሜሪካ ከኤርትራ እና ኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት ይበልጡኑ እየሻከረ የመጣው በሰሜን ኢትዮጵያ ከተቀሰቀሰው ጦርነት ጋር ተያይዞ ሲሆን ኢትዮጵያ የታላቁ ህዳሴ ግድብ የመጀመርያ ሙሌት ማሳካቷን ተከትሎ አሜሪካ የምታደርገውን የገንዘብ እርዳታዎች ማቆምን ጨምሮ ማዕቀብ የመጣል ማስፈራሪያዎችን ስታሰማ ቆይታለች። ይህም ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት ለመሻከሩ እንደዋነኛ ምክንያት ይጠቀሳል። 

የፌደራሉ መንግስት ከህወሓት ጋር በነበረው ግጭት የአሜሪካ መግስት በክልሉ ለተፈጸሙት የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የኢትዮጵያን እና የኤርትራ መንግስት ተጠያቂ አድርጓል። 

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን የኤርትራ መንግስት ጦሩን ከትግራይ ክልል ሙሉ በሙሉ እንዲያስወጣ በተደጋጋሚ ሲጠይቁ የቆዩ ሲሆን በመጨረሻም የአሜሪካ መንግስት በኤርትራ እና በኤርትራ የጦር አመራሮች ላይ ማዕቀብ ጥሏል። 

የኤርትራ መንግስት በበኩሉ አሜሪካ ህወሓትን በማገዝ ለአፍሪካ ቀንድ እና ለቀጠናው አለመረጋጋት አስተዋጾ እያደረገች እንደሆነ ክስ አቅርቧል።  

የማነ ገብረመስቀል ከፍተኛ የኤርትራ መንግስት ባለስልጣን ሲሆኑ በማህበራዊ ሚድያ በተለይም በይፋዊ የትዊተር ገጻቸው ላይ በተደጋጋሚ የአሜሪካ መንግስት ህወሓትን እየረዳ እንደሆነና ይህ ደግሞ ይበልጥ ለቀጠናው አለመረጋጋት በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ እንደሚያግዝ በመናገር ትችት ሲሰነዝሩ ቆይተዋል።  

በአስመራ የአሜሪካ ኤምባሲ በበኩሉ በይፋዊ የፌስቡክ ገፁ አማካኝነት የኤርትራ መንግስት በኢትዮጵያ ትግራይ ክልል የሰብዓዊ መብት ጥሰት እየፈጸመ እንደሆነ በመግለፅ፣ የማነ ገብረመስቀል ሀሰተኛ መረጃን በመፈብረክ በማህበራዊ ሚድያ እያሰራጩ እንደሆነ ገልጿል።      

የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ሲሆኑ የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኦስማን ሳሌህ ናቸው። ኦስማን ሳሌህ ከኤርትራ ውጭ በሚኖራቸው ጉዞ የፕሬዝዳንቱ አማካሪ የማነ ገብረአብ አብረዋቸው ይታያሉ።     

የማነ ገብረመስቀል የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት የቀድሞው የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር የሆኑት አሊ አብዱ ሀገራቸውን ክደው መጥፋታቸው ከታወቀ በኋላ እኤአ በ2015 ነበር።
በዚህም መሰረት የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር እንጂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እንዳልሆኑ በማረጋገጥ በዩቲዩብ ቻናሉ የተላለፈውን መረጃ ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል። 

ምስሉ በመንግስት ታጣቂዎች የወደመን የዘመነ ካሴን እናት ንብረት ያሳያል?

ከ150 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ግንቦት 23 ፤ 2014 ዓ.ም ላይ “ሰበር ዜና ‘ወያኔ ዘመነ ካሴ ኤርትራ በገባ ጊዜ እንዲህ የደካማ እናቱን ንብረት አላቃጠለም አልዘረፈም ነበር። ዛሬ የአብይ መንግስት በጭንቅ ጊዜ የራሱን ወንበር ብሎም ህዝብን የታደገውን የአርበኛ ዘመነ ካሴ እናት ልጅሽን አምጭ በማለት እንዲህ አውድሞታል።” የሚል ፅሁፍ በማያያዝ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። ዘመነ ካሴ የፋኖ መሪ እንደሆነ በተከታዎቹ ዘንድ የሚነገርለት ግለሰብ ነው።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከ 190 በላይ ግብረመልስ ሲያገኝ ከ65 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።  

ፋኖ ማለት ሀገር ለመጠበቅና ከጠላት ለመከላከል በበጎ ፈቃድኝነት የተሰባሰቡ የአማራ ወጣቶች የወል ስም ነው። በሰሜን ኢትዮጵያ የተነሳውን ጦርነት የትግራይ ኃይሎች በአጎራባች የአማራና የአፋር አካባቢዎች ባደረጉት መስፋፋት መንግስት ያቀረበውን የክተት ጥሪ ተቀብለው አያሌ የፋኖ አባላት ወደ ጦር ግንባር ዘምተዋል። በመንግስት በራሱ የታጠቁት የፋኖ አባላትም የህወሓት ኃይሎች የአማራን እና የአፋርን አካባቢዎችን ለቀው እስከወጡበት ጊዜ ድረስ ከሀገር መከላከያ ሰራዊት ጎን ተሰልፈው በውጊያ ተሳትፈዋል።

ታህሳስ 11 ቀን 2014 ዓ.ም የትግራይ ተዋጊ ሀይሎች በሰሜን ኢትዮጵያ ካሉ የትግራይ አካባቢዎች ለቀው መወጣታቸውን እና ከ13 ወራት ቆይታ በኋላ የተኩስ አቁም ስምምነትን ለማድረግ መወሰናቸውን አስታውቀዋል። 

መጋቢት 15 ቀን 2014 ዓ.ም የፌደራሉ መንግስት በትግራይ የተኩስ አቁም ስምምነት [ለሰብዓዊ እርዳታ ሲባል]አድርጓል።  በሰብዓዊ እርዳታ እጥረት ምክንያት ለሚጠፋው የሰው ልጅ ህይወትን ለመታደግ የፌደራሉ መንግስት ሰብዓዊ እርዳታን ግምት ውስጥ ያስገባ ተኩስ አቁም እንዲደረግ መወሰኑን አስታውቋል።

ይህን ተከትሎ ግንቦት 17 ቀን 2014 ዓ.ም የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በሰጠው መግለጫ “በአማራ ክልል ውስጥ ሁከት ፣ ብጥብጥ እና ስርዓት አልበኝነት በማስፈን ሕዝብ እንዳይረጋጋ እርስ በርሱ እንዲጋጭና አንድነቱን እንዲያጣ የሚያደርጉ ተግባራት በመፈፀም ራሳቸውን በአማራ ህዝብ ጉያ ውስጥ የወሸቁ ጠላቶችን ለማስቆም ጥረት እያደረገ እንደሆነ ገልፆ፣ እየተከናወነ ለሚገኘው የህግ የበላይነትን የማረጋገጥ መንግስታዊ ተግባር በዓላማው፣ በሂደቱም ሆነ በውጤቱ የሕዝብ እና የሀገር ደኅነነትን ለማረጋገጥ የታለመ መሆኑን በመገንዘብ መላው የአማራ ህዝብ ሕግ እና የሕግ የበላይነትን ለማስከበር ለሚደረገው ጥረት ሙሉ ውግንናውን በመስጠት ውስጣዊ አንድነቱን አጠናክሮ ሊያስቀጥል እንደሚገባ” ገልጿል።

ከዚህ በኋላ የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ አካውንቶች እና ድረ-ገፆች በፌደራል መንግስቱ እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ግጭት እንዳለ የሚያሳይ መረጃዎችን ሲያሰራጩ ነበር።  

እንደ ዋዜማ ሬድዮ ዘገባ ከሆነ የካቲት 27 ቀን 2014 ዓ.ም በምስራቅ ጎጃም ዞን ሞጣ ከተማ የፋኖ አመራር በመንግስት መታሰሩን ተከትሎ በፋኖ ታጣቂዎች እና በፊደራሉ መንግስት መካከል ግጭት ተከስቶ ነበር።   

የክልሉ መንግስት በበኩሉ ሁኔታውን የህግ ማስከበር ሂደት ነው በማለት ምላሽ የሰጠ ሲሆን ሁኔታው ክልሉን ለመረበሽ በሚንቀሳቀሱ ሀይሎች እንደተፈጠረ ገልጿል። የአማራ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ይልቃል ከፍያለ “መንግስት ፋኖን ማጥቃትም ሆነ ትጥቅ የማስፈታት አላማ እንደሌለው በማስረዳት ዘመቻው ትኩረት ያደረገው በክልሉ በህገወጥ የመሳርያ ዝውውር በግድያ እና በዝርፍያ የሚሳተፉ ሀይሎችን እንደሆነ ገልፀው ነበር። 

ይህ በእንዲህ እያለ መንግስት የፌደራል እና የክልል የፀጥታ አካላት በፋኖ አመራሮች ቤት በመግባት ማሰር እንደጀመሩ የሚናገሩ የተለያዩ ሪፖርቶች ወጥተዋል።    

ግንቦት 15 ቀን 2014 ዓ.ም My views on news የተባለ ድረ-ገፅ “ፋኖ ዘመነ ካሴ የፌደራል መንግስቱን አስጠነቀቀ” በሚል ርዕስ አንድ ፅሁፍ አስነብቦ ነበር።

የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶችም የፋኖ ዘመነ ካሴ ቤተሰብ ቤቶች እና ንብረቶች እንደወደሙ እና እንደተቃጠሉ ሲገልፁ ቆይተዋል። አንድ ከ180 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ “የዘመነ ካሴ ወንድም ንብረት ካሴ የ85 አመት እድሜ ያላቸው እናታቸው ቤትና ንብረት በመንግስት ታጣቂዎች እንደወደመ ገልጿል” በማለት መረጃውን አጋርቶ ነበር።   

ሀቅቼክ ያገኘው የፌስቡክ ፖስትም ይህን ሁኔታ ተገን በማድረግ የተለጠፈ ነበር። 

ሀቅቼክ ምስሉን ለማጣራት ባደረገው ጥረት ምስሉን ከ3 የተለያዩ ምስሎች ጋር ቀደም ባለ ጊዜ ተጋርቶ አግኝቶታል። ምስሉ ከዚህ ቀደም ጥር 15 ቀን ከ13ሺ በላይ ተከታይ ባለው የትዊተር አካውንት ላይ “ከአባይ ተሻግረው የመጡ ታጣቂዎች በሆሮ ጉድሩ ዞን የኦሮሞ ገበሬ ቤቶችን አቃጥለዋል” በሚል ርዕስ ተለጥፎ ነበር። 

የፋኖ ዘመነ ካሴ እናት ቤት እንደተቃጠለ የሚያሳዩ የተለያዩ መረጃዎች ቢኖሩም ይህ የፌስቡክ ፔጅ የተጠቀመው ምስል መረጃው በፌስቡክ ገፁ ከተጋራበት ጊዜ እጅግ ቀደም ብሎ የተላለፈና የተባለውን ዜና የማይደግፍና የተሳሳተ እንደሆነ ታውቋል።
ስለዚህ ሀቅቼክ መረጃውን ለመደገፍ ጥቅም ላይ የዋለውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።      

ሀሰት፡ ምስሉ በቅርቡ ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከመራራ ጉዲና ጋር መገናኘታቸውን አያሳይም

ከ25ሺ በላይ ተከታይ ያለው የትዊተር አካውንት ግንቦት 25 ቀን 2014 ዓ.ም ላይ “ኦባሳንጆ ከታላቁ የፖለቲካ ልሂቅ ፕርፌሰር መራራ ጉዲና ጋርም ስለ ሰላም መክረዋል!” በሚል የፅሁፍ መግለጫ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የትዊተር ፖስቱ ከ150 በላይ ግብረ መልሶችን ሲያገኝ ከ35 ጊዜ በላይ ሪትዊት ተደርጓል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

በህወሓት እና በፌደራል መንግስት መካከል የተቀሰቀሰው ጦርነት እስካሁን ድረስ ያልተፈታ ችግር ሆኗል። 

ከጥቂት ወራት በፊት ለሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት በሚል በፌደራሉ መንግስት የቀረበው የተኩስ አቁም ስምምነት በህወሓት ዘንድ ተቀባይነትን አግኝቶ የነበረ ሲሆን ይህ ስምምነት ለሰላም ንግግር እና ግጭቱን ለማቆም ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር ተገምቶ ነበር። 

የቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት የነበሩት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ነሀሴ 20 ቀን 2013 ዓ.ም የምስራቅ አፍሪካ ከፍተኛ ተወካይ ሆነው መሾማቸውን የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበር የሆኑት ሙሳ ፋኪ አሳውቀዋል። የምስራቅ አፍሪካ ከፍተኛ ተወካዩም በቀጠናው ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት ለማምጣት የሚሰሩ ይሆናል።

ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከመንግስት ሀላፊዎችና ከህወሓት አመራሮች ጋር ሰላማዊ መፍትሄ ለማምጣት በተደጋጋሚ ተገናኝተዋል። በጦርነት ውስጥ የሚገኙት ሁለቱም አካላት ጦርነት እንዲያቆሙና ወደ ድርድር እንዲመጡ ሀላፊነት ወስደው እየሰሩ ይገኛሉ። 

ግንቦት 23 ቀን 2014 ዓ.ም በአፍሪካ ቀንድ የአፍሪካ ኅብረት ልዩ መልዕክተኛ ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከህወሓት ሊቀመንበር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ጋር በመቀሌ ከተማ ተገኝተው ተነጋግረዋል። ከሁለት ቀናት በኋላም ለስራ ጉብኝት ከጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ ጋር ባሌ ሮቤ ተገኝተው ጉብኝት አድርገዋል። 

የትዊተር ፖስቱም ይህን አውድ ታሳቢ በማድረግ የተጋራ ነበር። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት ለማጣራት ባደረገው ምርመራ ምስሉ ከዚህ ቀደም የነበረና የቆየ  ሆኖ ያገኘው ሲሆን “የአፍሪካ ህብረት ምርጫ ታዛቢ ቡድን የበላይ ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሊቀ መንበር ዶ/ር መራራ ጋር ተገናኝተዋል።”በሚል በአፍሪካ ህብረት ይፋዊ ድረ ገጽ ላይ በሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ተጋርቶ አግኝቶታል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ የቲዉተር ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

የተቀናበረ፡ ምስሉ በትግራይ የተቀሰቀሰ አመፅን አያሳይም

ከ1100 በላይ ተከታይ ያለው የትዊተር አካውንት ግንቦት 16 ፤ 2014 ዓ.ም ላይ “ሰበር መረጃ’ በትግራይ ክልል አመፅ ተቀስቅሷል ፤ የትግራይ ህዝብ አብይ አህመድ ይምራን እያለ ነው” የሚል ፅሁፍ አያይዞ ሶስት ምስሎችን አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የትዊተር ፖስቱ ከ80 በላይ ግብረ መልሶችን ሲያገኝ ከ30 ጊዜ በላይ ሪትዊት ተደርጓል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሎቹን መርምሮ የተቀናበረ ብሏቸዋል።

በህወሓት እና በፌደራል መንግስቱ መካከል የተከሰተው ግጭት እስካሁን ድረስ መፍትሄ ያላገኘ ጉዳይ ሆኖ ቆይቷል።

ህወሓት ጦርነቱ እንዲያበቃ የተኛውንም አይነት የዲፕሎማሲያዊ መንገዶችን እንደሚከተል እና ያ የማይሆን ከሆነ ግን መልሶ ወደ ጦርነቱ ሊገባ እንደሚችል ተናግሯል። ህወሓት የሰብዓዊ እና የመድሃኒት እርዳታ ወደትግራይ ክልል እንዳይገባ የፌደራል እና የክልል መንግስታት እያገዱ ነው በማለት በተደጋጋሚ  ክስ ሲያቀርብ ቆይቷል።   

ግንቦት 12 ፤ 2014 ዓ.ም ህወሓት እንዳስታወቀው የትግራይ መንግስት የፖለቲካ ልዩነትን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ያለውን ቁርጠኛነት ለማሳየት ለአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ለሆኑት የቀድሞ የናይጄርያ ፕሬዝዳንት ኦሊሴጎን ኦባሳንጆ በገባው ቃል መሰረት 4208 የሚሆኑ የጦር እስረኞችን የፈታ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ 401 የሚሆኑት ሴቶች እንደሆኑ በመግለጫው አስታውቋል።

ጥር 5 ቀን 2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኢታዦማር ሹም የሆኑት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ “የትግራይ ህዝብ ለህወሓት ሲል ከዚህ በላይ መሞት የለበትም። በሺዎች የሚቆጠር ህይወት ጠፍቷል። የትግራይ ህዝብ ህወሓትን እምቢ ማለት አለበት።” ብለው ነበር። 

የትዊተር ፖስቱም ይህን አውድ ታሳቢ በማድረግ የተጋራ ነበር። 

ሀቅቼክ ምስሎቹን ለማጣራት ባደረገው ጥረት ሁለቱ ምስሎችDW አማርኛ የፌስቡክ ገፅ ላይ መስከረም 22 ቀን 2011 ዓ.ም በተጋራ ፖስት ላይ “ለደህንነታችን እንሰጋለን ያሉ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ሌሎች ተሳታፊዎች ዛሬ በመቐለ ሰልፍ አካሄዱ። ሰልፈኞቹ የደህንነት ስጋት ባለባቸው አካባቢዎች መማር እንደሚሰጉ በመግለፅ መንግስት መፍትሄ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።” በሚል ፅሁፍ ስር አግኝቶታል።

በሰልፉ ላይ “የተጋሩ ተማሪዎች ህይወት ያሳስበኛል፣ ዋስትና ወደሌለው ቦታ ልጆቻችን አንልክም፣ ተማሪዎች ትርጉም የሌለው መስዋእት መክፈል የለባቸውም፣ የክልል እና ፌደራል መንግስታት መፍትሄ ይስጡን” የሚሉ መፈክሮች ተስተጋብተዋል።

ምስል አንድ 

ምስል ሁለት

ሶስተኛው ምስል ሰኔ 20 ቀን 2010 ዓ.ም borkena.com በተባለ ድረ-ገፅ ላይ “Fresh ethnic-based violence in Asossa left at least eight people dead.” በሚል ፅሁፍ ስር አግኝቶታል። 

የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ምንጮችን በመጥቀስ የተፃፈው ይህ ዜና “የበርታ ተወላጅ ነን የሚሉ ወጣቶች በዚያ አካባቢ የሚኖሩ ሌሎች የአማራ እና ኦሮሞ ነዋሪዎች የሚያንቀሳቅሷቸው ቢዝነስ ተቋማት ላይ በተቀናጀ መልኩ ጥቃት ሰንዝረዋል። ይህን ተከትሎም የአማራ ተወላጆች የመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ እንዳደረጉ ቢሰማም ከበርታ ማህበረሰብ የተጎዳ ይኑር አይኑር የተጣራ መረጃ አልተገኘም” በማለት ያስነብባል።  

ምስል ሶስት       

የመጀመርያ ሁለቱ ምስሎች በትግራይ የነበረን ህዝባዊ ሰልፍ የሚያሳዩ ቢሆንም መረጃውን ለመደገፍ ምስሉ ተቀናብሯል። ከዚያ በተጨማሪ ሶስተኛው ምስል ደግሞ ከትግራይ ክልል እንዳልሆነ ተረጋግጧል።
ስለዚህ ሀቅቼክ ምስሎቹን መርምሮ እና አጣርቶ የተቀናበሩ እንደሆኑ አረጋግጧል።

ምስሎቹ ኢትዮጵያ የታጠቀቻቸውን C-130 ሄርኩሊዝ የጦር አውሮፕላኖችን ያሳያል?

አንድ የፌስቡክ ፖስት ግንቦት 7 ፤ 2014 ዓ.ም ኢትዮጵያ የታጠቀቻቸው C-130 ሄርኩሊዝ ጀቶች የሚል ፅሁፍን አያይዞ አምስት ምስሎችን አጋርቶ ነበር።

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ከ44 ጊዜ በላይ ሲጋራ ከ500 በላይ ግብረ መልሶችንም ማግኘት ችሎ ነበር።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን አጣርቶ መረጃውን በከፊል ሀሰት ብሎታል። 

በህወሓት እና በፌደራል መንግስቱ መካከል የተቀሰቀሰው ጦርነት እስካሁን ድረስ ያልተፈታ ችግር ሆኗል። 

ከጥቂት ወራት በፊት ለሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት በሚል በፌደራሉ መንግስት የቀረበውን የተኩስ አቁም ስምምነት በህወሓት ዘንድ ተቀባይነትን አግኝቶ የነበረ ሲሆን ይህ ስምምነት ለሰላም ንግግር እና ግጭቱን ለማቆም ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር ተገምቶ ነበር። 

የተኩስ አቁም ስምምነቱ ከታወጀ በኋላ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እና በህወሓት አመራር በሆኑት ደብረፅዮን ገብረሚካኤል መካከል የቀጥታ የስልክ ንግግር (ውይይት) ተደርጓል የሚሉ ያልተረጋገጡ ሪፖርቶች ሲወጡ ነበር።

በዩትዩብ በተለቀቀ አንድ የድምፅ መረጃ መሰረት የህወሓት ከፍተኛ የጦር አመራር የሆኑ አንድ ሰው ከታደሰ ወረደ ጋር በመሆን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኤታማጆር ሹም የሆኑት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላን በሞሪሽየስ አግኝተው እንዳወሯቸው ገልፀዋል። 

ነገር ግን ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከህወሓት አመራሮች ጋር ተገናኝተው ስለ መወያየታቸው የሚሰራጨውን መረጃ ሀሰት እና መሰረተ ቢስ መሆኑን ተናግረዋል።

ህወሓት በመግለጫዎቹ ግጭቱን ለማቆም ሰላማዊው መንገድ የማይሳካ ከሆነ በጦርነቱ እንደሚቀጥል ገልጿል

ህወሓት በተለያዩ ጊዜያቶች የፌደራል መንግስቱ እና የክልል ባለስልጣናት እርዳታ ወደ ትግራይ ክልል እንዳይገባ እየከለከሉ ነው በሚል በተደጋጋሚ የተለያየ ክስ ሲያቀርብ የቆየ ሲሆን አሁንም ወደ ትግራይ ክልል የደረሰው እርዳታ በቂ አለመሆኑን ተናግሯል።

ከሳምንታት በፊትም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትን በሁመራ በአካል ተገኝተው ጎብኝተዋል። 

ይህ በእንዲህ እንዳለ በአንፃሩ ህወሓት በተለያዩ የትግራይ ከተሞች የህዝብ ለህዝብ ውይይት አካሂዶ የነበረ ሲሆን የህወሓት አመራር የሆኑት ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ፤ ፈትለወርቅ ዘውዴ ፤ ጌታቸው ረዳ እና አለም ገብረዋህድ ተገኝተው ውይይቱን መርተውታል።

ግንቦት 2 ቀን 2014 ዓ.ም በተካሄደው በዚህ የህዝብ ውይይት ደብረጽዮን ገብረሚካኤል “ለሰላም ያደረገነው ጥረት ስላልተሳካ አሁን ለመጨረሻው የጦርነት ምዕራፍ እንድትዘጋጁ” በማለት ለህዝቡ ጥሪ አቅርበዋል።

በቅርቡ አዳዲስ የወረራ እና የግጭት ሪፖርቶች እየወጡ የሚገኙ ሲሆን ይህም ሁኔታ ሀገሪቷ በድጋሚ ሙሉ በሙሉ ወደ ጦርነት እንዳትገባ ስጋትን ፈጥሯል።

ከዚህ ጋር በተያያዘም ህወሓት የጦርነት ነጋሪት እየጎሰመ ነው በማለት ህወሓት ወደሌላ ጦርነት እንዳይገባ  የአውሮፓ ህብረት ጫና እንዲያደርግበት የፈደራሉ መንግስት ጠይቋል።  

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ኢትዮጵያ ያሏትን የC-130 ሄርኩሊዝ አውሮፕላን ጀቶችን ያሳያል በማለት አምስት ምስሎችን አጋርቷል። 

የአሜሪካ መንግስት ግንቦት 29 ፤ 2010 ዓ.ም ላይ C-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላኖችን ሀገሪቱ ለምታካሄደው የሰላም ማስከበር ተልዕኮ እንዲያግዛት ለኢትዮጵያ አስረክቧል። 

የፌስቡክ ፖስቱ ከተጠቀመባቸው ምስሎች መካከል አንዱ ይህ አሜሪካ ለኢትዮጵያ የለገሰችው የጦር አውሮፕላን ይገኝበታል። ይሁን እንጂ ከአምስቱ ምስሎች ቀሪዎቹ አራቱ የተወሰዱት ከሌላ እትሞች ሲሆን ኢትዮጵያ የታጠቀችውን C-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላኖችን አያሳዩም።   

ምስል አንድ

ሰኔ 24 ቀን 2006 ዓ.ም በአንድ የዩቲዩብ ቻናል ላይ የተለቀቀው ይህ ቪድዮ የAirbus A400M የጦር አውሮፕላን ያሳያል። 

ምስል ሁለት 

ምስሉ በየካቲት 21 ቀን 2010 ዓ.ም በአሜሪካ የመከላከያ ዲፓርትመንት ትዊተር ገፅ ላይ ከተለቀቀ ቪድዮ ላይ ተቆርጦ የተወሰደ ሲሆን ምስሉ የሚያሳየው በቅፅል ስሙ “የሞት መልዓክ” ወይም “Angel of Death” የተሰኘውን AC-130 የተባለ ሄርኩሊዝ የጦር አውሮፕላን ነው። 

ምስል ሶስት 

ምስሉ የተወሰደው በአሜሪካ የመከላከያ ዲፓርትመንት በኩል ከተለቀቀ ቪድዮ ሲሆን ከአሜሪካ መንግስት ለኢትዮጵያ የተሰጠውን የC-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላን ላይ ከአሜሪካ የመጡ ባለሙያዎች ለኢትዮጵያውያን አብራሪዎች እና ቴክኒሽያኖች ትምህርት እየሰጡ እንደሆነ የሚያሳይ ምስል ነው።

ምስል አራት 

ምስሉ በግንቦት 5 ቀን 2014 ዓ.ም በአንድ የዩቲዩብ ቻናል ላይ ከተለቀቀ ቪድዮ ላይ በመውሰድ የተጋራ ሲሆን ይህ የዩቲዩብ ቻናልም መስከረም 5 ቀን 2013 ዓ.ም ላይ ከተጋራ ሌላ የዩቲዩብ ቪድዮ ላይ የተወሰደ ነው። ቪድዮውም የአሜሪካውን C-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላንን ያሳያል። 

ምስል አምስት

እንደ ምስል አራት ሁሉ ምስል አምስትም ግንቦት 5 ቀን 2014 ዓ.ም ከተለቀቀ የዩቲዩብ ቪድዮ ላይ የተወሰደ ሲሆን ይህ የ ዩቲዩብ ቻናልም መስከረም 5 ቀን 2013 ዓ.ም ከተለቀቀ ሌላ የዩቲዩብ ቪድዮ ላይ የወሰደ ሲሆን ቪድዮው የአሜሪካውን C-130 ሄርኩሊዝ የጦር አውሮፕላን ጥንካሬን የሚያሳይ ነው።

ይሁን እንጂ የፌስቡክ ፓስቱን ለመደገፍ ከተጋሩት  ከአምስቱ ምስሎች መካከል አንዱ ምስል ብቻ የኢትዮጵያን C-130 የሚያሳይ ሲሆን የቀሩት አራት ምስሎችይህን አውሮፕላን አያሳዩም።
ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱን በከፊል ሀሰት ብሎታል።   

Exit mobile version