የተጣሩ መረጃዎች

ሀሰት ፡ ምስሉ የኦነግ ሸኔ ጦርን የተቀላቀሉ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን አያሳይም

ከ 70 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ግንቦት 6 ቀን 2014 ዓ.ም ላይ “በርከት ያሉ የመከላከያ ሰራዊት አባላት የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊትን መቀላቀላቸውን ሰምተናል” በሚል ፅሁፍ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።  

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከ200 በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ20 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል አጣርቶ ሀሰት ብሎታል። 

በፌደራል መንግስቱ ዘንድ ኦነግ ሸኔ እየተባለ የሚጠራው እና እራሱን ደግሞ የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት ብሎ የሚጠራው ወታደራዊ ቡድን እስከ ሚያዝያ 23 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ወታደራዊ ክንፍ ነበር። ከዚያ በኋላ እራሱን ከኦሮሞ ነፃነት ግንባር ተለይቶ የትጥቅ ትግልን አማራጩ አድርጓል። 

የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ፓርቲ ሚያዝያ 1 ቀን 2014 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ የፌዴራሉ መንግስት ከኦነግ ሸኔ ጦር ጋር እያደረገ ያለውን ግጭት በሰላማዊ መንገድ በመፍታት ሁለቱ ሀይሎች ወደ ሰላማዊው የፖለቲካ ምህዳር እንዲገቡ ጠይቋል። በተጨማሪም መንግስት ለትግራይ ክልል የሰጠውን የሰላም አማራጭ [ተኩስ አቁም] ዕድል ኦነግ ሸኔንም በተመለከተ እንዲተገበረው ጠይቋል።

ቅዳሜ መጋቢት 24 ቀን 2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት የደቡብ እዝ አመራር የሆኑት ኮሎኔል ግርማ አየለ በቡድኑ ላይ የማያዳግም እርምጃ እየተወሰደ እንዳለ ገልፀው ነበር። የፌዴራሉ መንግስት ከክልል ሀይሎች ጋር ባደረገው ጥምረት የተቀናጀ ጥቃት በቡድኑ ላይ እያደረሰ እንደሆነ ኮሎኔሉ ገልፀው ቡድኑ ዘርፏቸው የነበሩ መሳሪያዎች ጥይቶች እና የመድሃኒት አቅርቦቶች እንደተማረኩም አስታውቀዋል።  

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ባለፉት ሳምንታት በኦሮሚያ ክልል  በሰላማዊ ዜጎች ላይ የደረሱ የተለያዩ የጅምላ ጭፍጨፋዎች እና የአየር ጥቃቶች እንዳሉ የሚያሳዩ የተለያዩ ሪፖርቶች ወጥተዋል። 

የመከላከያ ሰራዊት፤ የፌደራል ፖሊስ አባላት እና ሪፐብሊካን ጋርዶች በዘር በመከፋፈል ወደ ኦነግ ሸኔ እየተቀላቀሉ ነው የሚል የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶችም ተስተውለዋል።

ወደ ኦነግ ሸኔ የተቀላቀሉ የሪፐብሊካን ጋርድ አባላት ሊንክ   

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በዘር እየተከፋፈሉ ኦነግ ሸኔን እየተቀላቀሉ ነው ሊንክ 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህንን አጋጣሚ እና ሁኔታን መሰረት አድርጎ የተጋራ ነው።    

ሀቅቼክ ምስሉን ለማጣራት ጥረት ያደረገ ሲሆን ምስሉ ከዚህ በፊት ጥቅምት 21 ቀን 2014 ዓ.ም ከ140 ሺህ በላይ ተከታይ ባለው የፌስቡክ ገፅ ላይ የተጋራ ሲሆን ከፎቶው ጋር የተያያዘው መግለጫ ፅሁፍም እንዲህ ይነበበባል “የአብይ አህመድ መከላከያ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ፈርሷል። በዚህም ከደሴ የተረፈው ኮምቦልቻ ከተማን ለቆ ወደ ከሚሴ ቢሄድም ከሚሴ ላይ ትጥቁን ለአካባቢው ህዝብ አስረክቦ ወደ መሀል ሀገር ለመሄድ፣ ማምለጫ መኪና አጥተው እየተንገላቱ ነው። እንደ አጋጣሚ ገንዘብ ያላቸው በኮንትራት መኪና ለሊት ወጥተው አምልጠዋል።” 

የፌደራል ሀይሎች መንግስትን ክደው ወደ ኦነግ ሸኔ እየተቀላቀሉ ነው የሚሉ የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶች ቢኖሩም የፌስቡክ ገፁ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመው ምስል የተሳሳተና የቀረበውን ሪፖርት የማያሳይ መሆኑ ታውቋል።

ይህም በመሆኑ ሀቅቼክ ምስሉን አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።  

ሀሰት: ምስሉ ደምቢዶሎ ዩኒቨርስቲን አያሳይም

ከ500 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ሚያዚያ 28 ቀን፣ “የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት ደምቢ ዶሎን መቆጣጠሩን ገለፀ” የሚል የፅሁፍ መግለጫ ያለው አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። መረጃውንም ለመደገፍ ከተቀመጡ ሦስት ምስሎች መሀል በአንደኛው ላይ “ደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ” በሚል በቀይ ቀለም ተፅፎበታል።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ3ሺ በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ 950 ጊዜ በላይ ተጋርቷል።

ቢሆንም ሀቅቼክ በቀይ ቀለም “ደምቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቲ” ተብሎ የተፃፈበትን ምስል ለማጣራት ባደረገው ምርመራ ምስሉ ደምቢዶሎ ዩንቨርሲቲን እንደማያሳይ አረጋግጧል።

ይህም በመሆኑ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።

የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት፣ የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦነግ) ወታደራዊ ክንፍ የነበረ ሲሆን ሚያዚያ 23 ፣ 2013 ዓ.ም ለሁለት ተከፍሏል። በኢትዮጲያ መንግስት “ኦነግ ሸኔ” እየተባለ የሚጠራው የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት በፓርላማ በአሸባሪነት ተፈርጇል።

የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት ከመንግስት ጋር በጦርነት ላይ ከሚገኘው ሕወሃት ጋር ጥምረት መፍጠሩን በነሀሴ 2012 አሳውቋል። 

የመንግስት ኮምኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር አቶ ለገሰ ቱሉ መጋቢት 24 ቀን 2014 ዓ.ም የኦሮሚያ ክልልና የፌደራል የፀጥታ ኃይሎች በተቀናጀና ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ በኦነግ ሸኔ ላይ እርምጃ እየወሰዱ እንደሚገኙ ገልፀዋል

በተጨማሪም መንግስት በምዕራብ ወለጋ በሚገኙት በነቀምት፣ በደምቢዶሎ እና በሌሎችም አከባቢዎች በኦነግ ሸኔ ላይ ጥቃት እየፈፀመ እንደሚገኝ የኮምኒኬሽን ሚኒስትሩ ገልፀዋል። 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህን ሁኔታ እና ወቅት በመጠቀም መረጃውን እንዲደግፍለት የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት በምዕራብ ወለጋ የሚገኘውን ደምቢዶሎ ከተማን መቆጣጠሩን ለማሳየት “ደምቢዶሎ ዩኒቨርስቲ” የሚል በምስል ላይ የተፃፈ ፅሁፍ አጋርቷል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት ለማጣራት ባደረገው ምርመራ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ በር የሚያሳየውን ምስል ከዚህ ቀደም ታህሳስ 12 ቀን 2010 ዓ.ም ላይ በቢቢሲ አማርኛ ዜና ‘በወለጋ ዩኒቨርሲቲ ሁለት ተማሪዎች ሞቱ’ በሚል ተጋርቶ አግኝቶታል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ሀሰት ፡ ምስሉ በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያ ሰራዊት የተማረኩ የጣልያን ወታደሮችን አያሳይም

ሚያዝያ 25 ቀን 2014 ዓ.ም አንድ የፌስቡክ ገፅ “በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያ ጦር የተማረኩ የጣልያን ወታደሮች” በሚል የፅሁፍ መግለጫ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ300 ጊዜ በላይ መጋራት ሲችል ከ አንድ ሺህ በላይ ግብረ መልስ ማግኘትም ችሏል። ሀቅቼክ ይህ ምስል የተካተተበት በመረጃ ማጣራት ፅሁፉን የዛሬ አመት ለንባብ አብቅቶ ነበር።

ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ ያቀረበውን መረጃ ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 

የአድዋ ጦርነት 1896 እአአ በጣልያን ወራሪ ኃይል እና በአጼ ሚኒሊክ በሚመራው በኢትዮጵያ ጦር መካከል የተደረገ ጦርነት ሲሆን በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል በሚገኘው አድዋ ከተማ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ እንደተከናወነ ታሪክ ያሳያል። 

ወራሪው የጣልያን ጦር በኤርትራ በኩል ወደ ደቡብ አቅጣጫ ተጉዞ ኢትዮጵያን ለመቆጣጠር ጥረት አድርጎ የነበረ ሲሆን በጀነራል ኦሬስት ባራቴሪ የሚመራውና ዘመናዊ መሳርያን የታጠቀው የጣልያን ጦር በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያውያን ሽንፈት ገጥሞታል። በጦርነቱም በቁጥር የበዙ የጣልያን ወታደሮችና ከጣልያኖች ጋር ሲሰሩ የነበሩ ቅጥረኛ ወታደሮች አብዛኞቹ ሲገደሉ የቀሩት ተማርከዋል።   

ይህ የፌስቡክ ፖስት የተጋራው 81ኛው የኢትዮጵያ አርበኞች ቀን ከሚከበርበት ከሚያዝያ 27 ቀን 2014 ዓ.ም ሁለት ቀናት በፊት ነበር። በየአመቱ ሚያዝያ 27 ቀን የሚከበረው የአርበኞች ቀን መታሰቢያነቱ ሚያዝያ 27 ፤ 1933 ዓ.ም የጣልያን ወረራ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ያበቃበትን እና የንጉስ አጼ ስላሴን ከስደት ወደ ሀገራቸው መመለሳቸውን ለመዘከር የሚከበር ብሄራዊ በዓል ነው። 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህን ወቅት እና ሁኔታ በመጠቀም በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያ ሰራዊት የተማረኩ የጣልያን ወታደሮች በማለት ምስሉን ሊያጋራ ችሏል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ምስሉ በጦርነቱ ወቅት በኢትዮጵያ ወታደሮች የተማረኩ የጣልያን ወታደሮችን እንደማያሳይ አረጋግጧል።

ምስሉ የተወሰደው በሚያዝያ ወር 1937 ዓ.ም አካባቢ በነበረ ሁነት ሲሆን ኢንሳይክሎፒድያን ጨምሮ የተለያዩ ድረ-ገፆች ላይ ይገኛል።

ምስሉ በመጀመሪያ በቀረበበት ድረ-ገፅ እንደተገለፀው ምስሉ የሚያሳየው በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወቅት በጀርመን ጫካዎች ውስጥ የተማረኩ የናዚ ወታደሮችን ሲሆን የአሜሪካ የ12ኛ ክፍለ ጦር አባል የሆነ አንድ ወታደር እነዚህን የጀርመን ወታደሮች ሲጠብቃቸው የሚያሳይ ምስል እንደሆነ ይናገራል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።       

ሀሰት: ምስሉ በቅርቡ በህገወጥ የመሬት ወረራ ተወስዶ ለእርሻ ስራ የዋለ ቦታን አያሳይም

ከ 2 ሚሊዮን በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ መጋቢት 26 ቀን፣ “በህገወጥ የሚወረረው ቦታ እያለቀ ሲመጣ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የወጣቶች ማዘውተርያ የሆኑ ሜዳዎችን ለገበሬ በሚል ሰበብ ለልዩ ጥቅመኞች እየታደለ ነው። ይሄ ሀያት አካባቢ ልጆች ሲጫወቱበት የነበረ ሜዳ ነው በንጋታው ሲመጡ ታርሶ ጠብቋቸዋል” የሚል የፅሁፍ መግለጫ ያለው አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።  

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ1500 በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ 156 ጊዜ በላይ ተጋርቷል።

ነገር ግን የፌስቡክ ፖስቱ ፅሁፉን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት አጣርቶ ሀሰት ሀቅቼክ ብሎታል።    

የቅርብ መረጃዎች በአዲስ አበባ ከተማ መጠነ ሰፊ ህገወጥ የመሬት ወረራ እንዳለ የጠቆሙ ሲሆን፤ በቃሊቲ ፣ በለሚ ኩራ፣ በቦሌ እና በንፋስ ስልክ ክፍለ ከተሞች ላይ በስፋት መስተዋሉንም ገልፀዋል።

በአንድ ተቃዋሚ ፓርቲ በጉዳዩ ላይ የሰራው ጥናት ግኝቶች መሰረት የመሬት ወረራው ግንባር ቀደም ተሳታፊዎች “ቦታዎቹ ከዚህ ቀደም የቤተሰቦቻችን መሬቶች በመሆናቸው በቂ ካሳ ሳይከፈለን ከቦታችን ተነስተናል” የሚሉ ግለሰቦች እና ወረራ በተፈፀመባቸው ቦታዎች አካባቢ የሚገኙ የክፍለ ከተማና የወረዳ ኃላፊዎችና ፈፃሚዎች አንደሆኑ በመጥቀስ ፣ “ጉዳዩን በማፋጠን ሕገ-ወጥ ደላላዎችም ተሳታፊዎች ነበሩ” ብሏል።

በፌስቡክ ገፁ የቀረበው መረጃም ይህን ሁኔታ መሰረት አድርጎ የቀረበ ነው። 

ሀቅቼክ የምስሉን ትክክለኛነት ለማጣራት ጥረት ያደረገ ሲሆን ምስሉ ከዚህ ቀደም ግንቦት 21 ቀን 2011 ዓ.ም “አዲስ አበባ የእግር ኳስ ሜዳዎቿ በ “ባለ ጊዜ ነን” ባዮች ወደ እርሻ ማሳነት እየተቀየሩ ነው” በሚል ርዕስ የወጣ ፅሁፍ አካል ሆኖ አግኝቶታል። 

ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ ፅሁፉን ለመደገፍ የተጠቀመው ምስል የቆየ እና ከመረጃው ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የሌለው መሆኑን አረጋግጧል።

ይህም በመሆኑ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል አጣርቶ ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል።  

ሀሰት ፡ ምስሉ ትግራይ ድንበር አካባቢ የሰፈሩ የኤርትራ ወታደሮችን አያሳይም

ከ100 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ መጋቢት 17 ቀን፣ “የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን ውሳኔ [ለሰብዓዊ እርዳታ ሲባል ተኩስ ማቆምን] ተከትሎ የኤርትራ ጦር ትግራይ ድንበር አካባቢ 13 ዘመናዊ ትጥቅ የታጠቀ ክፍለ ጦር ወደ ድንበር አስጠጋች” የሚል የፅሁፍ መግለጫ ያለው አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ1400 በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ 140 ጊዜ በላይ ተጋርቷል።

ነገር ግን ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ ፅሁፉን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።    

ጥር 25 ቀን 2014 ዓ.ም መንግስት ከህወሓት ጋር አየተደራደረ ነው ተብሎ የሚናፈሰውን መረጃ በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከፓርላማ ለተነሳላቸው ጥያቄ መልስ ሲሰጡ፣ “ስለ ድርድር ጉዳይ ብዙ ሲወራ ሰምቻለው ነገር ግን እስካሁን ድረስ ምንም አይነት ድርድር የሚባል ነገር የለም” በማለት ተናግረው ነበር።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸውም፣ “እስካሁን ድረስ ድርድር አላደረግንም ማለት እስከመጨረሻው ድረስ ንግግር(ድርድር) አናደርግም ማለት አይደለም ምክንያቱም ድርድር እና ንግግር ችግርን የመፍቻ አማራጮችን የምናይበት ነው” በማለት የመንግስትን አቋም አሳውቀዋል። 

መጋቢት 15 ቀን 2014 ዓ.ም የፌደራሉ መንግስት አስቸኳይ እና አላማውን የሰብዓዊ እርዳታ ተደራሽነት ላይ ያደረገ ግጭት ማቆም አውጇል። መንግስት በመግለጫው አንዳሳወቀው፣ ውሳኔው ወደትግራይ ክልል የሰብዓዊ እርዳታ ያለምንም ችግር ማድረስንና ህይወት ማዳንን ታሳቢ ያደረገ ነው። በመግለጫው መንግስት ካስቀመጣቸው ቅድመ ሁኔታዎች አማፂያኑ “ከማንኛውም የጦርነት እንቅስቃሴ እንዲቆጠቡ እንዲሁም ከተቆጣጠሯቸው አጎራባች አካባቢዎች ለቀው እንዲወጡ” አንዱ ነው።

ይህንን የፌደራሉን መንግስት ውሳኔ ተከትሎ ህወሓት በበኩሉ የትኛውንም አይነት ግጭት ለማቆም ተስማምቷል። 

ነገር ግን ይህ የዕርቅ ውሳኔ በሂደት ላይ ባለበት ሰዓት የመከላከያ ሰራዊት ትግራይ ድንበሮች አካባቢ እየተጠጋ እንደሆነ የሚያሳዩ የተለያዩ መረጃዎች ወጥተዋል። ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህን ሀሳብ መሰረት አድርጎ የተጋራ ነው።   

ሀቅቼክ የምስሉን ትክክለኛነት ለማጣራት ጥረት ያደረገ ሲሆን ምስሉ ከዚህ ቀደም ሀምሌ 26 ቀን 2011 ዓ.ም “ሳዋ-የብሄራዊ ቀን የብር እዮቤልዩ ክብረ በዓል” በሚል ርዕስ የታተመ ፅሁፍ አካል ሆኖ አግኝቶታል።  

ፅሁፉ ሳዋ ተብሎ የሚጠራው የኤርትራ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ማዕከል የነበረውን የብር እዮቤልዩ ክብረ በዓልንና የ32ተኛ ዙር ምልምል ሰልጣኝ ወታደሮች የተመረቁበት ሁነትን በማስመልከት የቀረበ የዜና ሪፖርት ነበር። 

የኤርትራ ጦር በትግራይ ድንበር አካባቢ ሰፍሯል የሚሉ የተለያዩ መረጃዎች ቢኖሩም ይህ የፌስቡክ ፖስት ፅሁፉን ለመደገፍ የተጠቀመው ምስል የቆየ እና ከመረጃው ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የሌለው ነው።

ይህም በመሆኑ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል አጣርቶ ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል።     

H.R. 6600 እና S.3199 የሚባሉት ረቂቅ ህጎች ፀድቀዋል? ሩሲያ እና ቻይናስ ህጎቹ እንዳይፀድቁ በድምፃቸው መሻር ይችላሉ?

ከሰሞኑ በተለያዩ የሶሻል ሚድያ አውታሮች ላይ H.R.6600 እና S.3199 በተባሉ ረቂቅ ህጎች የአሜሪካው የህግ መወሰኛ ምክር ቤት የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ያለውን ግጭት እንዲያቆም ለማስገደድ ውሳኔ እንዲሰጥባቸው አቅርቧል። እነዚህን ረቂቅ ህጎች በተመለከተ በማህበራዊ ሚድያው ላይ በስፋት ሲዘዋወሩ የነበሩ ፖስቶች እና አሳሳች ሪፖርቶች ተስተውለዋል።

ሀቅቼክ ከነዚህ ህጎች ጋር በተያያዘ ሀሰተኛ እንዲሁም አሳሳች የሆኑ መረጃዎች እና ሪፖርቶችን ተመልክቷል። አንዳንድ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶችም S.3199 የተባለው ረቂቅ ህግ እንደፀደቀ አድርገው መረጃ ሲያስተላልፉና ሲያዘዋውሩ ሰንብተዋል።

ሌሎች ደግሞ H.R.6600 የተባለው ህግ በሩሲያ እና በቻይና ተቃውሞ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብታቸውን ተጠቅመው ውሳኔውን ሊያቋርጡት እንደቻሉ አስነብበዋል።  

እነዚህን ሀሰተኛ እና አወዛጋቢ መረጃዎችን በጥቂቱ ለማሳየት ያክል :- 

የረቂቅ ህጎቹ አላማ ምንድን ነው? 

የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ገፆች ላይ የተንፀባረቁት ኃሳቦች ይህን የሚመስሉ ሲሆን በህጎቹ ዙሪያ የሚቀርቡ መረጃዎችን ትክክለኝነት ለመረዳት በአሜሪካ የህግ መወሰኛ ምክር ቤት የቀረቡት እነዚህ ህጎች ምንድን ናቸው፣ ህግ ሆነው የሚፀድቁበት ሂደትስ ምን ይመስላል የሚለውን መገንዘብ አስፈላጊ ነው።

HR6600 ረቂቅ ህግ በኢትዮጵያ ውስጥ መረጋጋትን ፣ ሰላምን እና ዴሞክራሲን ለማምጣት ጥር 27 ቀን 2014 ዓ.ም ተዋወቀ። የአሜሪካ ሴኔት አባል በሆነው ቶም ማልኖውስኪ አነሳሽነት እንዲሁም የህግ መወሰኛ ምክር ቤት አባል በሆኑት ማይክል ማኮውል እና ግሪጎሪ ሚክስ ደጋፊነት የቀረበው ይህ ረቂቅ ህግ በሰሜን ኢትዮጵያ ያለውን ግጭት ለማቆም በኢትዮጵያ መንግስትና በግጭቱ ተሳትፎ ያላቸው አካላት ላይ ጫና ማሳደርን እሳቤ ያደረገ የህግ ማዕቀፍ ነው።    

ይህ ረቂቅ ህግ ከፀደቀ ንብረቶችን ማገድ፣ የቪዛ ክልከላ እንዲሁም ከአሜሪካ እና አለም አቀፍ ከሆኑ ተቋማት የእርዳታ ክልከላ እንዲደረግ ያስችላል።  

ሌላኛው ረቂቅ ህግ S.3199  ጥቅምት 25 ቀን 2014 ዓ.ም በአሜሪካ የሴኔት አባል በሆነው ሮበርት ሜንዴዝ አነሳሽነት የተዋወቀ ነው።  ይህ ረቂቅ ህግ እንደ ህግ ከፀደቀ በሰሜን ኢትዮጵያ ባለው ግጭት ላይ ተሳታፊ የሆኑ ወገኖችን በገንዘብ እንዲሁም በጦር መሳሪያ የሚደግፉ አካላት ላይ ማዕቀቦችን  ለመጣል የሚያስችል ህግ ነው። 

S.3199 ህግ በዋነኝነት ለኢትዮጵያ እና ኤርትራ መንግስት ከአለም አቀፍ ተቋማት የሚሰጡ ማንኛውም አይነት የብድር እንዲሁም የብድር ማራዘሚያዎችም ሆነ የትኛውንም አይነት የፋይናንስ እና ቴክኒካል ድጋፎች ላይ ክልከላ የሚያደርግ ህግ ነው። 

የመንግስት አቋም

የነዚህ ረቂቅ ህጎች ጉዳይ በኢትዮጵያ የማህበራዊ ሚድያ አውታሮች ላይ በሰፊው አወዛጋቢ እና አወያይ ሀሳብ ሆኖ ቆይቷል። በአሜሪካና በተለያዩ የአለም ክፍሎችም ህጎቹን በመቃወም ሰልፎች የተደረጉ ሲሆን፣ በተቃራኒው ደግሞ የረቂቅ ህጎቹን መፅደቅ የሚያበረታቱ የተቃውሞ ሰልፎችም ተደርገዋል።

ረቂቅ ህጎቹን በማስመልከት መጋቢት 13 ቀን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ አቶ ደመቀ መኮንን ውጭ ሀገራት ላሉ የኢትዮጵያ ዲያስፖራዎች H.R.6600 እና S.3199 ረቂቅ ህጎችን በመቃወም ሰልፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።  

በተጨማሪም መጋቢት 15 ቀን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ ዲና ሙፍቲ ውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ረቂቅ ሰነዶቹ እንዳይፀድቁ የሚያደርጉትን ተቃውሞ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል።  

በቅርቡም በአሜሪካ ዋሺንግተን ዲሲ የHR6600 እና S3199 ረቂቅ ህጎችን በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ ተደርጎ ነበር።

ህጎቹ እውን ፀድቀዋል? አሜሪካና ቻይናስ ህጉን መሻር ይችላሉ?

ረቂቅ ህጎቹን በተመለከተ በማህበራዊ ሚድያ አውታሮች ሲዘዋወሩ ከነበሩት ኃሳቦች አንዱ ረቂቅ ህጎቹ እንዳይፀድቁ በሩሲያ እና ቻይና አማካኝነት ውድቅ መደረጉን የሚያሳዩ ነበሩ። 

ይሁን እንጂ እነዚህ ረቂቅ ህጎች በአሜሪካ መንግስት ምክር ቤቶች የቀረቡ በመሆናቸው በአሜሪካ በብሄራዊ ደረጃ ብቻ የሚፀድቁ ይሆናል። እነዚህ ረቂቅ ህጎች በተባበሩት መንግስታት ኤጀንሲዎች እና በአለም አቀፍ ስምምነቶች ደረጃ የሚወሰኑ ማዕቀቦች አይደሉም። 

ይህም በመሆኑ ሩሲያም ሆነ ቻይና ያላቸውን ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ሊጠቀሙ የሚችሉት በተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ባላቸው መቀመጫና ስልጣን ብቻ ሲሆን፣ በአንፃሩ እነዚህ H.R.6600 እና S.3199 ረቂቅ ህጎች በአሜሪካ መንግስት ደረጃ የቀረቡ በመሆናቸው የህጎቹ መፅደቅ ላይ ምንም አይነት መብትና ስልጣን አይኖራቸውም። 

ሁለተኛው እና አወዛጋቢ ጉዳይ የነበረው የS3199 ረቂቅ ህግ በቅርቡ ህግ ሆኖ ፀድቋል የሚል ነበር።

እነዚህ ሁለቱ ረቂቅ ህጎች ህግ ሆ 5 የተለያዩ ደረጃዎችን ማለፍ ይኖርባቸዋል። እነዚህም ለውጭ ጉዳዮች ኮሚቴ መተዋወቅ፣ በሴኔቱ መፅደቅ በመቀጠልም በምክር ቤቱ መፅደቅ ያለበት ሲሆን በመጨረሻም በፕሬዝዳንቱ ከፀደቀ በኋላ ህግ መሆን ይችላሉ። 

በሌላ መልኩ ረቂቁ በሴኔት አባል አማካኝነት የቀረበ ከሆነ በሴኔቱ የውጭ ግንኙነቶች ኮሚቴ አማካኝነት ድምፅ ተሰጥቶበት ወደ ሙሉ ሴኔት የሚተላለፍ ይሆናል። ነገር ግን ይህ ረቂቅ በተወካዮች ምክር ቤት አባል የቀረበ ከሆነ በውጭ ግንኙነቶች ኮሚቴ አማካኝነት ድምፅ ተሰጥቶበት ወደ ሙሉ የተወካዮች ምክር ቤት ይተላለፋል።

ከነዚህ በአሜሪካ ረቂቅ ህጎችን የማፅደቅ ሂደት አንፃር ስንመለከተው፣ S3199 ረቂቅ ህግ የቀረበው በሴናተር አማካኝነት ነው። በሴኔቱ የውጭ ግንኙነቶች ኮሚቴ አማካኝነት ረቂቁ መጋቢት 20 ቀን 2014 ዓ.ም በሴኔቱ ድምፅ እንዲሰጥበት ተላልፏል። ይህ ረቂቅ ህግ ሆኖ እንዲጸድቅ በሴኔቱ፣ በተወካዮች ምከር ቤት እና በአሜሪካው ፕሬዝደንት መፅደቅ አለበት። ይህ ረቂቅ ህግም ወደ ፕሬዝደንቱ ከማለፉ በፊት በሴኔቱ እና በተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት የሁለቱን ድምፅ ማግኘት አለበት።

በሌላ በኩል HR6600 የሚባለው ረቂቅ ህግ የተዘጋጀው በተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት ነው። ይህ ረቂቅም የካቲት 1 ቀን 2014 ዓ.ም በውጭ ጉዳይ ተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት ድምፅ ተሰቶበት ወደ አሜሪካ ተወካዮች ምክር ቤት ተላልፏል። በተመሳሳይ ሁኔታም ይህ ረቂቅ ህግ በተወካይ በሴናተሮች ፀድቆ በመጨረሻም በፕሬዝዳንቱ አማካኝነት ወደ ህግ መቀየር ይኖርበታል። 

ከዚህ መመልከት እንደምንችለው እነዚህ ሁለት ረቂቅ ህጎች እስካሁን ህግ ሆነው አልፀደቁም። በመሆኑም እነዚህ ረቂቅ ህጎች በሂደት ላይ ያሉ ሲሆኑ ህግ ሆነው እንዲፀድቁ ሶስት ሂደቶችን፤ ማለትም በሴኔቱ፣ በተወካዮች ምክር ቤት፣ እና በመጨረሻም በፕሬዝደንቱ ሊፀድቅ ይገባዋል።

ሀሰት፡ ምስሉ በኤርትራ የአየር መቃወሚያዎች ተመቶ የወደቀን አውሮፕላን አያሳይም

ከ110ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የትዊተር አካውንት “ከሱዳን የጦር መሳሪያ ጭኖ በኤርትራ የአየር ክልል ወደትግራይ ክልል ሲበር የነበረ አንቶኖቭ አውሮፕላን በኤርትራ የአየር መቃወሚያዎች ዶግ አመድ ሆኖ ወደ መሬት ሲበተን” የሚል ጽሁፍን በማያያዝ መጋቢት 7 ቀን ላይ አንድ ምስልን አጋርቶ ነበር።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የምስሉን ትክክለኛነት አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።

በፌደራል መንግስት እና በህወሓት መካከል የተከሰተው ግጭት ለብዙዎች መፈናቀል ፣ ሞት እና መሰደድ ምክንያት ሆኗል። 

ሕዳር 5 ቀን ፤ 2013 ዓ.ም ከትግራይ ክልል ወደ ኤርትራ ዋና ከተማ አስመራ ሶስት ሮኬቶች እንደተተኮሱ የሚያሳዩ መረጃዎች አሉ።

ህዳር 24 ቀን ፤ 2014 ዓ.ም የሱዳን ሉዓላዊ ም/ቤት መሪ የሆኑት አብድልፈታ አልቡርሃን ከሱዳኑ አልሃዳት ቴሌቪዥን ጋር በነበራቸው ቆይታ የሱዳን መንግስት ህወሓትን እንደማይደግፍ የገለጹ ሲሆን ኢትዮጵያ ወስዳብናለች ያሉትን መሬት በጦርነት ሳይሆን በውይይት እንደሚፈቱት ተናግረዋል።  

ይህ የትዊተር ፖስትም ኢትዮጵያ አሁን ላይ ያለችበትን የእርስ በርስ ግጭት እና ሱዳን ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን የውዝግብ መቼት መረጃውን ለመፍጠር ተጠቅሞበታል። 

ሀቅቼክ ምስሉን ለመመርመር ባደረገው ጥረት ፎቶውን በአንድ AEROPRESS BG በተባለ የዩቱብ ቻናል ላይ አግኝቶታል። ይህ የዩቱብ ቻናል ከ2ሺህ በላይ ሰብስክራይበሮች ያሉት ሲሆን፣ “የካርጎ ማመላለሻ የነበረው Boeing 747-400 በአፍጋኒስታን ውስጥ ተከስክሷል” የሚል ጽሁፍን አያይዞ በሚያዝያ 22 ፤ 2005 ዓ.ም ይህን ቪድዮ አጋርቶ ነበር።

እንደ Wikipedia መረጃ ከሆነ ይህ Boeing 747-400 የተባለው አውሮፕላን አሁንም ለጭነት ማመላለሻነት እያገለገለ ይገኛል። 

የዚህን ቪድዮ ዝርዝር መረጃን በሚያዝያ 24 ፤ 2005 ዓ.ም በ CNN  ቴሌቪሽን ላይ የሚገኝ ሲሆን እንደ CNN የዜና ሪፖርት መሰረት በአውሮፕላኑ የመከስከስ አደጋ ሰባት አሜሪካኖች ሲሞቱ ስድስቱ ከሚቺጋን አንዱ ከኬንታኪ የመጡ የአሜሪካ ዜግነት ያላቸው ዜጎች መሆናቸው ተረጋግጧል። 

የመከስከሱ አደጋ የተፈጠረበት ቦታ በአፍጋኒስታን የሚገኝ እና ቤግራም የተባለ የአሜሪካ የአየር ሀይል ቤዝ ነበር። 

ይህ የትዊተር ፖስትም ምስሉን ከዚህ ቪድዮ ላይ ቆርጦ በመውሰድ ሊጠቀምበት ችሏል። ስለዚህ ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።             

ሀሰት ፡ ምስሉ በታላቁ የህዳሴ ግድብ ሰራተኞች ላይ ጥቃት ያደረሱ የጉሙዝ ታጣቂዎችን አያሳይም

ከ290 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ “የህዳሴ ግድቡ ንብረት አመላላሽ የነበሩ ሰራተኞች በጉዞ ላይ እያሉ በጉሙዝ ታጣቂዎች ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል” የሚል ፅሁፍን በማያያዝ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከ10 ሺህ ጊዜ በላይ ግብረመልስ ያገኘ ሲሆን ከ1200 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የምስሉን ትክክለኛነት መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 

ታላቁ የህዳሴ ግድብ በአፍሪካ ትልቁ የውሃ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ሲሆን ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ እስከ 6450 ሜጋዋት ሃይል ያመነጫል። ግድቡ ከሱዳን በስተምስራቅ 48 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልላዊ መንግስት በምትገኘው ጉባ ላይ እየተገነባ ያለ ግዙፍ ፕሮጀክት ነው።   

በየካቲት 23 ፤ 2009 ዓ.ም የኢትዮጵያ የኮምዩኒኬሽን ሚኒስትር ዴኤታ እንደተናገሩት የጸጥታ ሀይሎች በቤንሻንጉል ክልል በህዳሴ ግድቡ አቅራቢያ ከቤንሻንጉል ክልል አማጽያን ጋር ግጭት ውስጥ ገብተው ነበር።”

የተለያዩ የዜና ምንጮችም በግጭቱ 13 የሚሆኑ የአማጽያኑ አባላት እንደተገደሉ አስነብበዋል። አማጽያኖቹ የተለያዩ ፈንጂዎችን ፣ ቦምቦች እና ልዩ ልዩ የጦር መሳሪያዎችን ይዘው እንደነበረ የሚያሳዩ የተለያዩ ሪፖርቶች አሉ። 

በሚያዝያ 7 ፤ 2009 ዓ.ም ብዙ ቢልየን ዶላሮች ፈሰስ በተደረገበት በዚህ ግዙፍ የውሃ ሃይል ማመንጫ ፕሮጀክት አካባቢ ጥቃት ፈጽመው በነበሩት 10 የሚደርሱ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ህዝቦች ንቅናቄ አማጽያን ላይ ፍርድ ቤት ብይን ሰቷል። 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህን ሀሳብ ላይ መሰረት አድርጎ የተጋራ ነው። 

ሀቅቼክ ይህ የፌስቡክ ፖስት የተጠቀመውን ምስል በተለያዩ ፅሁፎች ላይ አግኝቶታል። ለምሳሌ ይህ ምስል በነሃሴ 26 ፤ 2009 ዓ.ም International Business Times  በተባለ ድረ-ገፅ ላይ የ26 ዓመቱ አሜሪካዊ ጋዜጠኛ ክሪስቶፈር አለን ደቡብ ሱዳን ውስጥ በነበረ ግጭት ምክንያት ተገድሎ መገኘቱን የሚያሳይ ጽሁፍ ይዞ ወቷል። 

ምስሉም በደቡብ ሱዳን ያሉ አማጽያንን የሚያሳይ ሲሆን እነሱም አብረው ከሚዋጉ ጓዶቻቸው ጋር ለመመሳሰል እንዲረዳቸው በጭንቅላታቸው ላይ ቀይ ጨርቅ እንደሚያስሩ ይህ ፅሁፍ ያስነብባል።     

የጉሙዝ ታጣቂዎች በግድቡ አቅራቢያ ጥቃትን እንደከፈቱ የሚያሳዩ የተለያዩ መረጃዎች ቢኖሩም አብዛኞቹ የፌስቡክ ገጾች ይህንኑ ምስል ተጠቅመዋል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገጾቹ የተጠቀሙትን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 

አሳሳች፡ ሩስያ በኢትዮጵያ የኒውክለር ኃይል ማመንጫ እንጂ የኒውክለር የጦር መሳሪያ ማምረቻ የማቋቋም ዕቅድ የላትም

አንድ የፌስቡክ ገፅ የካቲት 30 ፤ 2014 ዓ.ም በሰበር ዜና መልክ “ሩስያ በኢትዮጵያ ትልቁን የኒውክለር ማብላያ ልትከፍት ነው” በሚል ፅሁፍ የከባድ ሚሳኤሎች ምስል አጋርቶ ነበር።

 

ከጥቂት ሳምንታት በፊት በሩስያ እና በዩክሬን መካከል ግጭት ተከስቷል። ይህ የተከሰተውን ግጭት ተከትሎ በኔቶ እና በሩስያ መካከል የኒውክለር ጦርነት ሊከሰት ይችላል የሚሉ ስጋቶች ባሉበት ሁኔታ ይህ መረጃ ተጋርቷል።

ሚያዝያ ወር 2011 ዓ.ም ሩስያ በኢትዮጵያ በቀጣዮቹ አስር አመታት ውስጥ የኒውክለር ኃይል ማመንጫ ለመገንባት ከስምምነት ላይ ደርሳለች።

በታህሳስ 2013 ዓ.ም የኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የኒውክለር ኃይልን ለሰላማዊ አላማ በማዋል ዙርያ ከሩስያ ጋር የተደረገውን ስምምነት አፅድቋል። በመጋቢት ወር 2014 ዓ.ም ኢትዮጵያ እና ሩስያ የኒውክለር ኃይልን ለሰላማዊ መንገድ በመጠቀም ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።

ይህ የፌስቡክ ፖስት አሳሳች ከሆነበት ምክንያት አንዱ በፅሁፉ ካቀረበው ኃሳብ ጋር በጣም ትልልቅ እና ዘመናዊ ሚሳኤሎችን የሚያሳይ ምስልን ማያያዙ ነው። አብዛኛው ሰው የኒውክለር ማብላያ መገንባት የሚለውን ሀሳብ እንደ ኒኩሌር መሳሪያ ቢቆጥረውም ሩስያ ከኢትዮጵያ ጋር የገባችው ስምምነት ግን የኒውክለር መሳርያ ማምረቻን ለመገንባት ሳይሆን የኒውክለር ኃይል ማመንጫ ጣብያ ለመገንባት ነው።  

በአዲስ አበባ የሩስያ ኤምባሲ ለሀቅቼክ በኢሜል እንደገለፀው የተደረገው ስምምነት ኢትዮጵያን በተለያዩ የኒውክለር ቴክኖሎጂ ዘርፎች ተጠቃሚ እንድትሆን እንደሚያስችላት ገልጸዋል። 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ትልልቅ የሚሳኤል ምስሎችን በማያያዝ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ካለው ስምምነት በራቀ መልኩ የኒውክለር ጦር መሳሪያ ማምረቻ ጣቢያ ሊቋቋም እንደሆነ አስነብቧል። 

ከዚህም በተጨማሪ ሀቅቼክ ምስሉን በማጣራት ምስሉ የተወሰደው በመስከረም ወር 2012 ዓ.ም  በChina Central Television (CCTV) ላይ ከተላለፈ ቪድዮ እንደሆነ አረጋግጧል። ቪድዮው በመስከረም 19 ፤ 2012 ዓ.ም የቻይናው ኮሚኒስት ፓርቲ ከፈረንጆቹ ጥቅምት 1 ፤ 1949 ጀምሮ ስልጣን የያዘበትን 70ኛ አመት ክብረ በዓል በሚያከብርበት ቀን የተደረጉ ወታደራዊ ትርኢቶችን ያሳያል።  

በፌስቡክ ፖስቱ ላይ የተመለከቱት ከባድ ሚሳኤሎችም የተወሰዱት ከዚሁ ወታደራዊ ትርኢት ላይ ነው። ሚሳኤሉ DF (Dongfeng) ሲባል ትርጉሙ በመንደሪን ቋንቋ ‘ሚሳኤል’ ማለት ነው። 

ይህ 5B ሞዴል የሆነው የሚሳኤል አይነት እጅግ ውስብስብና አህጉር አቋራጭ ባልስቲክ ሚሳኤል ነው።  

የተለያዩ መረጃዎች የሚገኙበት እና Britannica የሚባለው ድረ-ገጽ ይህ ባልስቲክ ሚሳኤል ትልልቅ ፈንጂዎችን በተጨማሪም የኬሚካል ፣ የባዮሎጂካል ወይም የኒኩሌር መሳርያዎችን ሊሸከም እንደሚችል ያስነብባል።

ይህን ቪድዮ ካስተላለፉት የዜና አውታሮች መካከል አንዱ የሆነው CGTN በወታደራዊ ትርኢቱ ላይ የታዩት Dongfeng-5B የተባሉት ባልስቲክ ሚሳኤሎች የኒኩሌር ሚሳኤል እንደሆኑ ዘግቧል።

ይሁን እንጂ የፌስቡክ ፖስቱ ካቀረበው ሩስያ በኢትዮጵያ የኒውክለር ማብላያ ጣቢያ ልትገነባ ነው ከሚለው መረጃ አንፃር፣ የባልስቲክ ሚሳኤሉን የሚያሳየው ምስል የፌስቡክ ፖስቱን አሳሳች የሚያደርገው ሲሆን መረጃውን ለመደገፍ የታዩት ባልስቲክ ሚሳኤሎችም የሩስያ ሳይሆኑ የቻይና እንደሆኑ ተረጋግጧል።

ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱን አጣርቶ አሳሳች ብሎታል።          

ሀሰት፡ ምስሉ በቅርቡ በጨለንቆ የተደረገን ህዝባዊ ሁነት አያሳይም

126ተኛው የአድዋ ድል በዓል በሚከበርበት የካቲት 23 ፤ 2014 ዓ.ም ቀን ላይ ከ46 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው አንድ የፌስቡክ ገጽ “ጨለንቆ ላይ የምኒሊክ አረመኔነት ታስቦ ውሏል” በሚል ጽሁፍ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።

ይህ ጽሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከአንድ ሺህ በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ217 ጊዜ በላይ ደግሞ መጋራት ችሏል።

 ይሁን እንጂ ይህ የፌስቡክ ገጽ የተጠቀመው ምስል በ2007 ዓ.ም The Oromian Economist ከተባለ ድረ-ገጽ ላይ የተወስደ እንደሆነ ሀቅቼክ አረጋግጧል። 

126ተኛው የአድዋ ድል በዓል የካቲት 23 ቀን በመላው ኢትዮጵያ ተከብሮ ውሏል። ይህ የአድዋ ድል የመታሰቢያ ቀን በመዲናዋ አዲስ አበባም በአድዋ ድልድይ እና ሚኒሊክ አደባባይ በተለያዩ ሁነቶች ተከብሮ ውሏል። 

የኦሮሞ መብት ተከራካሪዎች አያሌ የኦሮሞ ሰማዕታት በጨለንቆ ጦርነት ላይ ለነፃነት ፣ ከጥገኝነት ለመላቀቅ ፣ ለፍትህ እና ለሰብዓዊነት እንደተዋደቁ ይናገራሉ። የጨለንቆ ጭፍጨፋ የመታሰቢያ ሀውልት ምርቃት የተከናወነው በመጋቢት 12 ፤ 2007 ዓ.ም በምስራቅ ሀረርጌ ነበር።

የጨለንቆ ጦርነት የተካሄደው በጥር ወር 1879 ዓ.ም በሸዋው ንጉስ አጼ ምኒልክ እና በሀረሩ ኢሚር አብደላህ ሁለተኛው መካከል ነበር። በጦርነቱ የሸዋው ንጉስ አጼ ሚኒሊክ  የሀረሩን ኢሚር አብደላ አሸንፈዋል። 

   

ሀቅቼክ ባደረገው ምርመራ እንዳረጋገጠው The Oromian Economist “በመጋቢት 12 ፤ 2007 ዓ.ም የጨለንቆ ጭፍጨፋ የመታሰቢያ ሀውልት ምረቃ” በሚል ርዕስ በቀረበ ፅሁፍ ውስጥ ይህን ምስል ተጠቅሞት ነበር። ይህ የዜና ሪፖርትም ከምርቃቱ ሁነት ላይ የነበሩ የተለያዩ ምስሎች እና ቪድዮዎችን አያይዞ አጋርቶ ነበር። 

በዚህም መስረት ያቀረበውን ሪፖርት ለመደገፍ የፌስቡክ ገጹ የተጠቀመበትን ምስል ወቅታዊነት አጣርቶ ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል።  

Exit mobile version