ይህ ቪዲዮ በትግራይ የተከሰተ ረሃብ ያሳያል?

ህዳር 18 2016 አንድ የፌስቡክ ገጽ በትግራይ የተራበ ጨቅላ ህጻን ነው በማለት ይህንን ቪድዮ አጋርቷል። ይህ ጽሁፍ እስከታተመበት ጊዜ ድረስ ቪዲዮው ወደ 8,000 የሚጠጋ እይታን ያገኘ ሲሆን ከ121 ጊዜ በላይም ተጋርቷል።

ከዚሁ ቪዲዮ ጋር ተመሳሳይ የሆኑ ልጥፍች በሌሎች የፌስቡክ ገጾች ላይም ተጋርተዋል። ተመሳሳይ ቪዲዮ በሌላ የፌስቡክ ገጽ ላይ ወደ 5,000 የሚጠጋ እይታን ያገኘ ሲሆን ከ80 ጊዜ በላይም ተጋርቷል።

በኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ከፍተኛ ድርቅ እና የረሃብ ቀውስ መከሰቱን መረጃዎች ያመለክታሉ። በአበርገለ ወረዳ ብቻ ከ19,000 ሄክታር ሰብል 17,000 ሄክታር ሰብል ለድርቅ መጋለጡን የትግራይ ክልል ግዝያዊ መንግስት አስታውቋል።

የአሜሪካ ዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲ (ዩ ኤስ ኤድ) እና የተባበሩት መንግስታት የአለም የምግብ ፕሮግራም (ዳብልዩ ኤፍ ፒ) በመንግስት ባለስልጣናት የእርዳታ ስርቆትን ክስ በመጥቀስ ዕርዳታውን አቁሟል።

በህዳር 3፣ 2016 ዩናይትድ ስቴትስ ዓለም አቀፍ ልማት ኤጀንሲ (USAID) ከስድስት ወራት እገዳ በኋላ በኢትዮጵያ የምግብ ዕርዳታ ስርጭትን በታህሳስ ወር እንደሚቀጥል አስታውቋል።

በ2016 ጥቅምት 20 የወጣው የኦቻ ዘገባ ከ5 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በአማራ እና በትግራይ ክልል በድርቅ መሰል ሁኔታዎች ተጎጂ ሆነዋል ብሏል።

በተጨማሪም የትግራይ ክልል አስተዳደር በወጀራትና አጽቢ ወረዳ ድርቅና ረሃብ መከሰቱን ገልጿል

ከሰሞኑ በትግራይ ክልላዊ መንግስት አበርገሌ ወረዳ ከፍተኛ ረሃብ እንዳለ በማህበራዊ ድረ-ገጾች ላይ አየተጋራ ቆይቷል።

በተጨማሪ እነዚህ ልጥፎች በትግራይ ክልል ለሚኖሩ ሰዎች የገንዘብ ማሰባሰብያ የማህበራዊ ሚዲያ ዘመቻዎችን ጀምረዋል።

በረሃብ የገንዘብ ማሰባሰብያ ዘመቻ መካከል አንድ የተራበ ጨቅላ ሕፃንን የሚያሳይ ቪዲዮ በማህበራዊ ሚዲያ በሰፊው ሲጋራ ነበር።

ነገር ግን ትክክለኛው ቪዲዮ ከሶስት ሳምንት በፊት ማለትም ህዳር 2፣ 2016 በቲክቶክ ላይ ተጋርቶ ተገኝቷል። 

የተጋራው ቪዲዮ በመጀመሪያ ካቶ ኒኮደም በተባለ የቲክ ቶክ አካውንት ላይ ተጋርቶ ተገኝቷል። ይህ የቲክ ቶክ አክውንት 1.8 ሚሊዮን ተከታዮች ሲኖሩት 34.5 ሚሊዮን የሚሆን ግብረመልስን አጊንቷል።

ይህ ኒኮደም የተባለ ግለሰብ በዩጋንዳ ወላጅ አልባ ህጻናትን የሚረዳ ለትርፍ ያልተቋቋመ ድርጅት መሪ እንደሆነ ይገልጻል። ለዚህ ሃሰተኛ መረጃ ጥቅም ላይ የዋለውን ቪዲዮ ጨምሮ ሌሎችም በዚህ ግለሰብ የቲክቶክ አካውንት ላይ እንክብካቤ እያገኙ ያሉ ሕፃናትን የሚያሳዩ ተመሳሳይ ቪዲዮዎችን በተደጋጋሚ ይጋራሉ።

ይህንኑ ህጻን ልጅ የሚያሳዩ ሌሎች ቪዲዮዎች እንዲሁ በዚሁ የቲክቶክ አካውንት ላይ ተጋርተዋል

ኒኮደም በ ጎፈንድሚ ላይ ባወጣው የገቢ ማሰባሰቢያ ልጥፍ ላይ “ሴቭ አፍሪካን ቻይልድ 254 ሚኒስትሪ (Save African Child 254 Ministry)” የተባለ በኡጋንዳ ወላጅ አልባ ሕፃናትን የሚረዳ ድርጅት እና “ኪንደር ሂልፈዘንትረም (Kinderhilfezentrum)” የተባለ ሌላ ግበረ-ሰናይ ድርጅት መስራች እንደሆነ ገልጿል።

በተጨማሪም “ኒኮላስ ሰቡፉ” ትክክለኛ ስሙ እንደሆነ እና “ካቶ ኒቆዲም” ቅፅል ስሙ መሆኑን ገልጿል

በትግራይ ክልል ድርቅና የረሃብ ችግር መከሰቱን ዘገባዎች ቢያመለክቱም ይህ ቪዲዮ ግን በትግራይ የተራበ ሕፃንን የሚያሳይ አይደለም። 

ስለዚህም ሀቅቼክ ይህን የፌስቡክ ፖስት ትክክል ያልሆነ ቪዲዮ በመጠቀሙ ሀሰት ብሎታል።

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከጎረቤቶቿ ድምር ይበልጣል?

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከአምስት አመት በፊት ከምስራቅ አፍሪካ በምጣኔ ሀብት ሁለተኛ ደረጃ ላይ የነበረችው ኢትዮጵያ  አሁን ከጎረቤቶቿ ሀገራት ኢኮኖሚ ድምር የላቀ ኢኮኖሚ አላት በማለት ተናግረዋል

ጠቅላይ ሚኒስትሩ እአአ በመጋቢት 2018 ሰፊ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ብልጽግናን እና ዲሞክራሲን ለማጎልበት ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ማሻሻያዎችን ቃል ገብተዋል። በብልጽግና ፓርቲ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስትም ማሻሻያው ሀገሪቱን በከፍተኛ ደረጃ አሻሽሏል ሲል ይገልጻል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ በትክክለኛው የኢኮኖሚ አቅጣጫ ላይ እንደምትገኝ እና ኢኮኖሚዋም እያደገ መምጣቱን በተደጋጋሚ የተናገሩ ሲሆን  በቅርቡ፣ የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) ባለፉት አምስት ዓመታት በእጥፍ ጨምሯል ያሉትም ከነዚህ መካከል የሚጠቀስ ነው።

ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ አህመድ በቅርቡ ለክረምት ተማሪዎች በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ እያደገች መሆኗን የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከጎረቤቶቿ ጋር በማነፃፀር ለተማሪዎቹ አብራርተዋል፡፡

ጠ/ሚንስትሩ  እንደተናገሩት፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በአጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) ልኬት ከአምስት ዓመታት በፊት ከኬንያ ቀጥሎ በምስራቅ አፍሪካ ሁለተኛው  ነበር። እ.ኤ.አ. በ2018 የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት መጠን 84.4 ቢሊዮን ዶላር ነበር፤ እንዲሁም የኬንያ ማዕከላዊ ባንክ እንደገለጸው፣ የሀገሪቷ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት መጠን  91.2 ቢሊዮን ዶላር ነበር።

ከአምስት ዓመታት በኋላ እአአ በ2022 የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት መጠን 126.8 ቢሊዮን ዶላር ሲደርስ፤ የኬንያ ደግሞ 119.5 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል። በዚህም የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) ከአምስት አመት በኋላ የኬንያን በልጦ ከምስራቅ አፍሪካ አንደኛ ሆኗል።

ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከጎረቤቶቿ ድምር እንኳን ይበልጣል ወይም የኢትዮጵያ ጎረቤት ሀገራት ኢኮኖሚ ተደምሮ ከኢትዮጵያ አንሷል በማለት ያስተላለፉት መረጃ ሀሰት ነው።

ኢትዮጵያ በአለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ባላቸው ስድስት ሀገራት ማለትም፡ ሶማሊያ፣ ኬንያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሱዳን፣ ኤርትራ እና ጅቡቲ እና እውቅና ባላገኘችው ሃገር ሶማሊላንድ ትዋሰናለች።

እንደ አለም ባንክ ዘገባ የሱዳን አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት እ.ኤ.አ. በ2022 51.7 ቢሊዮን ዶላር ነበር። በዚህም መሰረት የኬንያ እና የሱዳንን የሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) ተደምረው ከኢትዮጵያ (171.2 ቢሊዮን እና 126.8 ቢሊየን ሲነጻጸር) ይበልጣሉ።

የሱዳን፣ የደቡብ ሱዳን፣ የኤርትራ፣ የጅቡቲ፣ የሶማሌላንድ እና የሶማሊያ የቅርብ ጊዜ ኢኮኖሚ መረጃ በየራሳቸው ማዕከላዊ ባንኮች ወይም የስታስቲክስ ኤጀንሲዎች መረጃ ቋት ላይ አይገኝም። ስለዚህ እንደ አይኤምኤፍ ካሉ ሌሎች አለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ያወጡትን መረጃ አስደግፈን አቅርበናል።

የአለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) እ.ኤ.አ. በ2022 የበርካታ የአፍሪካ ቀንድ ሀገራት አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ)  አሃዞችን የዘገበ ሲሆን እነዚህም  አሃዞች እንደሚከተለው ናቸው፡- የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት 120.37 ቢሊዮን ዶላር፣ የኬንያ 113.7 ቢሊዮን ዶላር፣ የሱዳን 33.75 ቢሊዮን ዶላር፣ የሶማሊያ 10.42 ቢሊዮን ዶላር፣ የደቡብ ሱዳን 8.54 ቢሊዮን ዶላር፣ እንዲሁም የጅቡቲ 3.66 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል።  ይህ የአይኤምኤፍ መረጃ ግን ስለ ኤርትራ እና ሶማሌላንድ ለተጠቀሰው አመት መረጃን እንደማያጠቃልል ልብ ሊባል ይገባል።

ስለዚህ በ2022 የአምስቱ የኢትዮጵያ ጎረቤት ሀገራት (ኤርትራ እና ሶማሌላንድን ሳይጨምር) አጠቃላይ  ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት መጠን 170 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን ይህም ከኢትዮጵያ ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት መጠን  120.37 ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ነው።

ይህም ሲጠቃለል ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) ያላት ቢሆንም፣ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ  የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከጎረቤቶቿ ድምር የበለጠ ነው ማለታቸው እ.ኤ.አ. በ2022 የኢኮኖሚ መረጃን መሰረት በማድረግ ሀሰት ሆኖ ተገኝቷል።

የቆዩ የማኅበራዊ ሚዲያ መልዕክቶች ላይ አርትዖት መስራት ፤ አዲሱ የሀሰተኛ መረጃ ስርጭት ስልት

የፌደራሉ መንግስት የክልል ልዩ ሀይሎችን ትጥቅ በማስፈታት እንደፍላጎታቸው ወደመከላከያ ፤ ፌደራል እና የክልል ፖሊስ እንዲቀላቀሉ ውሳኔ ማሳለፉን ተከትሎ በአማራ ክልል ግጭት መከሰቱ ይታወሳል። ይህ በክልሉ የተከሰተው ግጭት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ይበልጥ እየተባባሰ እና ጉዳት እያስከተለ መምጣቱን የሚያሳዩ ሪፖርቶች እየወጡ ይገኛሉ።

ይህን ተከትሎ አማራ ክልል በፌደራል መንግስት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የተካሄዱ የተለያዩ ግጭቶችን እና ጦርነቶችን እያስተናገደ ይገኛል። በክልሉ ባለው ግጭትም የሰው ልጅ ህይወት ሲጠፋ የተለያዩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችም እንደተካሄዱ የሚያሳዩ የተለያዩ ሪፖርቶች እየወጡ ይገኛሉ።         


በሰኔ ወር የፋኖ ታጣቂዎች ጎንደር እና ደብረታቦርን ጨምሮ በአማራ ክልል የሚገኙ ዋና ዋና ከተማዎችን ተቆጣጥረው እንደነበር ይታወሳል። ይህን ሁኔታ ተከትሎ በክልሉ የተከሰተው ችግር  ክልሉ ባለኝ አቅም ልገታው አልችልም በማለት የፌደራሉ መንግስት ጣልቃ እንዲገባ እና መፍትሄ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርቧል። ከጥሪው በፊት በክልሉ የተወሰኑ አከባቢዎች ይንቀሳቀስ የኢፌድሪ መከላከያ ሰራዊት የክልሉን ጥሪ ተከትሎ በክልሉ በርካታ ቦታዎች ላይ ወታደሮቹን አሰማርቷል። በክልሉ የተከሰተውን ሁኔታ በዘላቂነት ለመቆጣጠር ያግዝ ዘንድ የኢፌድሪ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በአማራ ክልል ላይ ተፈፃሚነት እንዲኖረው ማፅደቁ ይታወሳል።

የፌደራል መንግስት ሀይሎች መጀመሪያ አካባቢ ስኬታማ የነበሩ ሲሆን በፋኖ ታጥቂዎች ስር የነበሩ የተለያዩ ከተማዎችንም መልሶ መቆጣጠር ችለው ነበር። ይሁን እንጂ አሁንም በክልሉ ላለው ግጭት ዘላቂ መፍትሄ ማግኘት ያልተቻለ ሲሆን ይህም ተጨማሪ ግጭቶች እና አመፆች በክልሉ እንደሚቀጥሉ ተጨባጭ ስጋት አለ፡፡

ከአማራ ብሄር ተወላጆች እስር ጋር ተያይዞ እየወጡ ያሉ ሪፖርቶች 

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በአማራ ክልል ከታወጀበት ከሐምሌ 28 ፤ 2015 ዓ.ም ጊዜ ጀምሮ የፌደራሉ መንግስት የአማራ ብሄር ተወላጆችን ጨምሮ ፖለቲከኞችን ፤ ጋዜጠኞችን እና ተፅዕኖ ፈጣሪዎችን አስሯል።

ከእነዚህም መካከል የቀድሞው የአማራ ክልል ምክር ቤት እና የገዥው ፓርቲ ብልፅግና አባል የነበሩት አቶ ዮሃንስ ቧያለው እንዲሁም የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) አመራር እና የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ክርስትያን ታደለ ለእስር ከተዳረጉት ጥቂት የአማራ ብሄር ተወላጆች ውስጥ ይጠቀሳሉ። 

እንደ መንግስት ሚድያዎች የዜና ዘገባ ከሆነ የፌደራሉ መንግስት 764 የሚሆኑ በክልሉ ያለውን የትጥቅ እንቅስቃሴ ይደግፋሉ ያላቸውን ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ይፋ አድርጓል።   


ይሁን እንጂ የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ሪፖርቶች መንግስት የአማራ ብሄር ተወላጆችን ኢላማ አድርጎ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች በሚገኙ የእስራ ማቆያ ቦታዎች እንዳሰራቸው እየተናገሩ ይገኛሉ።

ከዚህ ጉዳይ ጋር ተያይዘው እየወጡ ያሉ የማህበራዊ ሚድያ ላይ ፖስቶች በመንግስት እስር ላይ የሚገኙ የአማራ ብሄር ተወላጆችን የሚያሳዩ ናቸው በመባል እየተሰራጩ ይገኛሉ።

ለምሳሌ ያክል በመስከረም 2 ፤ 2016 ዓ.ም አንድ የፌስቡክ ገፅ (ከስር ያለውን ስክሪን ሾት ይመልከቱ) አራት ምስሎችን በማያያዝ ምስሎቹ በመንግስት አማካኝነት ከአዲስ አበባ ወጣ ብላ በምትገኘው ቱሉ ዲምቱ ከተማ ውስጥ በእስር ላይ የሚገኙ የአማራ ብሄር ተወላጆችን እንደሚያሳይ ከሚገልፅ ፅሁፍ ጋር አጋርቶ ነበር። ከዚህ በተጨማሪም ይህ የፌስቡክ ፖስት በካምፕ ውስጥ የሚገኙ እስረኞች ተላላፊ በሆኑ በሽታዎች እየተጠቁ እንደሆነም ገልጿል።  


[የመግለጫ ፅሁፍ ፡ እነዚህ በቱሉ ዲምቱ ካምፕ በእስር ላይ የሚገኙ እና በተላልፊ በሽታዎች የተጠቁ የአማራ ክልል ተወላጆች ናቸው]

ይህ ፖስት ብዙዎች ጋር መድረስ የቻለ ሲሆን ብዙ ግብረመልሶችንም ማግኘት ችሎ ነበር። ነገር ግን ሀቅቼክ ከዚህ ጋር ተያይዞ በቂ መረጃዎችን ማግኘት ስላልቻለ የምስሎቹን እርግጠኛነት ማጣራት አልቻለም።

የቆዩ ፖስቶችን ኤዲት ማድረግ

በሌላ በኩል አንዳንድ የመንግስት ደጋፊ የሚመስሉ የማህበራዊ ሚድያ አካውንቶች የዚህን ፌስቡክ ፖስት እና ስክሪን ሾት በማጋራት ምስሎቹ ከአመት በፊት እንደተጋራ ገልፀው ከአማራ ብሄር ተወላጆች እስር ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር እንደሌለ በመናገር ሲያጋሩ ቆይተዋል።

እነዚህ ፖስቶች የመጡት ምስሎቹ ሀሰተኛ እና መንግስት አሁን ያሰራቸውን የአማራ ክልል ተወላጆች እንደማያሳዩ ለማሳየት ነው።


(የመግለጫ ጽሁፍ ፡ እነዚህ ፖስቶች የተሳሳተ መረጃን ለማስተላለፍ ሀሰተኛ እና የቆዩ ምስሎችን ተጠቅመዋል)

ከስር ካለው ፌስቡክ ፖስት ላይ የተወሰደው ምስል (ስክሪን ሾት) የቆየ የፌስቡክ ፖስት ላይ የተጨመረ  ሲሆን ይህን አወዛጋቢ ምስል ለመጀመሪያ ጊዜ የተጋራው እዚህ ላይ ነው ለማስባል ይህ የፌስቡክ ገፅ ተጠቅሞበታል።         

 
(የመግለጫ ፅሁፍ፡ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ከመቶ በላይ ለሚሆኑ ጎዳና ተዳዳሪዎች የህክምና አገልግሎት ሰጥቷል)

ሀቅቼክ ምስሎቹ እና የፌስቡክ ላይ ልጥፎቹ ከአንድ አመት በፊት መጋራታቸውን ለማጣራት ጥረት አድርጓል። ሀቅቼክም ሰኔ 22 ፤ 2014 ዓ.ም የተጋራ አንድ የፌስቡክ ፖስት እነዚህን ምስሎች ከአማርኛ የመግለጫ ፅሁፍ ጋር አጋርቶት እንደነበረ ማስተዋል ችሏል።

ኤዲት ተደርጎ (ተቀይሮ) የነበረው የፌስቡክ ፖስት


ሀቅቼክ የቆየ ምስሎች ናቸው ተብሎ የተጋራበት የፌስቡክ ፖስት በቅርቡ የተቀየረ እንደሆነ እንዲሁም ምስሉም ከፅሁፉ ጋር አብሮ የተቀየረ መሆኑን አረጋግጧል።

ይህ የፌስቡክ ፖስት ለመጀመሪያ ጊዜ ሰኔ 22 ፤ 2014 ዓ.ም በኦሮሚኛ ፅሁፍ ተጋርቶ የነበረ ሲሆን በመግለጫውም አምስት ግድያ የተፈፀመባቸውን እና ታላቅ ስብዕና አላቸው ያላቸውን ሰዎች የጠቀሰበት ፖስት ሲሆን እነሱም ጆን ኤፍ ኬኔዲ ፤ ማርቲን ሉተር ኪንግ ፤ አብርሃም ሊንከን ፤ ማልኮም እና ሃጫሉ ሁንዴሳ ነበሩ።   

     
ይህ ፖስትም ሰኔ 22 ፤ 2012 ዓ.ም የተገደለውን ታዋቂውን የኦሮሚኛ ሙዚቃ አቀንቃኝ አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ከሌሎቹ አራት ሰዎች ጋር ያወዳደረብት የኦሮሚኛ ፅሁፍ ነበር። በመጀመሪያ የተጋራው ፖስት አንድ ምስል ብቻ እንደነበረው ማየት ይቻላል ነገር ግን ምስሉ ኤዲት ተደርጎ ስለወጣ እና በሌሎቹ ምስሎች ስለተተካ ሀቅቼክ የመጀመሪያውን ምስል ማግኘት አልቻለም።  

(ይህ ስክሪን ሾት ፡ ኦሪጅናሉን እና በኦሮሚኛ ፅሁፍ ተጋርቶ የነበረውን የሚያሳየው የፌስቡክ ፖስት ነው) 

ይሁን እንጂ ይህ የፌስቡክ ፖስት መስከረም 2 ፤ 2016 ዓ.ም እንደተቀየረ ያሳያል የኦሮሚኛ ፅሁፉም በሌላ የአማርኛ ፅሁፍ እንዲሁም አንድ የነበረው ምስል በሌሎች አምስት ምስሎች ተቀይሯል።

የተቀየረው እና አዲሱ ፖስት የሚያሳየው ፅሁፍ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ከመቶ ለሚበልጡ የጎዳና ላይ ነዋሪዎች ነዋሪዎች የህክምና አገልግሎት እየሰጠ ነው የሚል መግለጫ ነው።  

(መስከረም 2 ፤ 2016 ዓ.ም ላይ የመግለጫ ፅሁፉ እንደተቀየረ እና አምስት ምስሎች እንደተጨመረበት ያሳያል)  

በዚህ ምክንያት ሀቅቼክ ይህንን የፌስቡክ ፖስት ሐሰት ብሎታል። ይህ ፖስት ሆን ተብሎ እና ሰዎችን ለማሳስት እንደተቀየረ በግልፅ ማየት ይቻላል። 

ሀቅቼክ የማህበራዊ ሚድያ ተጠቃሚዎች ከእነዚህ አይነት አሳሳች የሆኑ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶች መጠንቀቅ እንዳለባቸው ያሳስባል።

በተለይም ፌስቡክ ከፈረንጆቹ 2013 ጀምሮ ተጠቃሚዎች የሚያጋርቱን መልዕክት ላይ የአርታዖት ስራ እንዲሰሩ፣ ተመልሰው እንዲያስተካክሉ የሚፈቅድ አማራጭ ይፋ ማድረጉ ተከትሎ ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል። ተጠቃሚዎችም መረጃዎች የተጋሩበትን ቀን ከማየት ባለፈ የፖስቱን ኤዲት ሂስትሪ(የተጋራውን መልዕክት የአርትዖት ታሪክ) ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል።     

H.R. 6600 እና S.3199 የሚባሉት ረቂቅ ህጎች ፀድቀዋል? ሩሲያ እና ቻይናስ ህጎቹ እንዳይፀድቁ በድምፃቸው መሻር ይችላሉ?

ከሰሞኑ በተለያዩ የሶሻል ሚድያ አውታሮች ላይ H.R.6600 እና S.3199 በተባሉ ረቂቅ ህጎች የአሜሪካው የህግ መወሰኛ ምክር ቤት የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ያለውን ግጭት እንዲያቆም ለማስገደድ ውሳኔ እንዲሰጥባቸው አቅርቧል። እነዚህን ረቂቅ ህጎች በተመለከተ በማህበራዊ ሚድያው ላይ በስፋት ሲዘዋወሩ የነበሩ ፖስቶች እና አሳሳች ሪፖርቶች ተስተውለዋል።

ሀቅቼክ ከነዚህ ህጎች ጋር በተያያዘ ሀሰተኛ እንዲሁም አሳሳች የሆኑ መረጃዎች እና ሪፖርቶችን ተመልክቷል። አንዳንድ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶችም S.3199 የተባለው ረቂቅ ህግ እንደፀደቀ አድርገው መረጃ ሲያስተላልፉና ሲያዘዋውሩ ሰንብተዋል።

ሌሎች ደግሞ H.R.6600 የተባለው ህግ በሩሲያ እና በቻይና ተቃውሞ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብታቸውን ተጠቅመው ውሳኔውን ሊያቋርጡት እንደቻሉ አስነብበዋል።  

እነዚህን ሀሰተኛ እና አወዛጋቢ መረጃዎችን በጥቂቱ ለማሳየት ያክል :- 

የረቂቅ ህጎቹ አላማ ምንድን ነው? 

የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ገፆች ላይ የተንፀባረቁት ኃሳቦች ይህን የሚመስሉ ሲሆን በህጎቹ ዙሪያ የሚቀርቡ መረጃዎችን ትክክለኝነት ለመረዳት በአሜሪካ የህግ መወሰኛ ምክር ቤት የቀረቡት እነዚህ ህጎች ምንድን ናቸው፣ ህግ ሆነው የሚፀድቁበት ሂደትስ ምን ይመስላል የሚለውን መገንዘብ አስፈላጊ ነው።

HR6600 ረቂቅ ህግ በኢትዮጵያ ውስጥ መረጋጋትን ፣ ሰላምን እና ዴሞክራሲን ለማምጣት ጥር 27 ቀን 2014 ዓ.ም ተዋወቀ። የአሜሪካ ሴኔት አባል በሆነው ቶም ማልኖውስኪ አነሳሽነት እንዲሁም የህግ መወሰኛ ምክር ቤት አባል በሆኑት ማይክል ማኮውል እና ግሪጎሪ ሚክስ ደጋፊነት የቀረበው ይህ ረቂቅ ህግ በሰሜን ኢትዮጵያ ያለውን ግጭት ለማቆም በኢትዮጵያ መንግስትና በግጭቱ ተሳትፎ ያላቸው አካላት ላይ ጫና ማሳደርን እሳቤ ያደረገ የህግ ማዕቀፍ ነው።    

ይህ ረቂቅ ህግ ከፀደቀ ንብረቶችን ማገድ፣ የቪዛ ክልከላ እንዲሁም ከአሜሪካ እና አለም አቀፍ ከሆኑ ተቋማት የእርዳታ ክልከላ እንዲደረግ ያስችላል።  

ሌላኛው ረቂቅ ህግ S.3199  ጥቅምት 25 ቀን 2014 ዓ.ም በአሜሪካ የሴኔት አባል በሆነው ሮበርት ሜንዴዝ አነሳሽነት የተዋወቀ ነው።  ይህ ረቂቅ ህግ እንደ ህግ ከፀደቀ በሰሜን ኢትዮጵያ ባለው ግጭት ላይ ተሳታፊ የሆኑ ወገኖችን በገንዘብ እንዲሁም በጦር መሳሪያ የሚደግፉ አካላት ላይ ማዕቀቦችን  ለመጣል የሚያስችል ህግ ነው። 

S.3199 ህግ በዋነኝነት ለኢትዮጵያ እና ኤርትራ መንግስት ከአለም አቀፍ ተቋማት የሚሰጡ ማንኛውም አይነት የብድር እንዲሁም የብድር ማራዘሚያዎችም ሆነ የትኛውንም አይነት የፋይናንስ እና ቴክኒካል ድጋፎች ላይ ክልከላ የሚያደርግ ህግ ነው። 

የመንግስት አቋም

የነዚህ ረቂቅ ህጎች ጉዳይ በኢትዮጵያ የማህበራዊ ሚድያ አውታሮች ላይ በሰፊው አወዛጋቢ እና አወያይ ሀሳብ ሆኖ ቆይቷል። በአሜሪካና በተለያዩ የአለም ክፍሎችም ህጎቹን በመቃወም ሰልፎች የተደረጉ ሲሆን፣ በተቃራኒው ደግሞ የረቂቅ ህጎቹን መፅደቅ የሚያበረታቱ የተቃውሞ ሰልፎችም ተደርገዋል።

ረቂቅ ህጎቹን በማስመልከት መጋቢት 13 ቀን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ አቶ ደመቀ መኮንን ውጭ ሀገራት ላሉ የኢትዮጵያ ዲያስፖራዎች H.R.6600 እና S.3199 ረቂቅ ህጎችን በመቃወም ሰልፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።  

በተጨማሪም መጋቢት 15 ቀን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ ዲና ሙፍቲ ውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ረቂቅ ሰነዶቹ እንዳይፀድቁ የሚያደርጉትን ተቃውሞ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል።  

በቅርቡም በአሜሪካ ዋሺንግተን ዲሲ የHR6600 እና S3199 ረቂቅ ህጎችን በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ ተደርጎ ነበር።

ህጎቹ እውን ፀድቀዋል? አሜሪካና ቻይናስ ህጉን መሻር ይችላሉ?

ረቂቅ ህጎቹን በተመለከተ በማህበራዊ ሚድያ አውታሮች ሲዘዋወሩ ከነበሩት ኃሳቦች አንዱ ረቂቅ ህጎቹ እንዳይፀድቁ በሩሲያ እና ቻይና አማካኝነት ውድቅ መደረጉን የሚያሳዩ ነበሩ። 

ይሁን እንጂ እነዚህ ረቂቅ ህጎች በአሜሪካ መንግስት ምክር ቤቶች የቀረቡ በመሆናቸው በአሜሪካ በብሄራዊ ደረጃ ብቻ የሚፀድቁ ይሆናል። እነዚህ ረቂቅ ህጎች በተባበሩት መንግስታት ኤጀንሲዎች እና በአለም አቀፍ ስምምነቶች ደረጃ የሚወሰኑ ማዕቀቦች አይደሉም። 

ይህም በመሆኑ ሩሲያም ሆነ ቻይና ያላቸውን ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ሊጠቀሙ የሚችሉት በተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት ባላቸው መቀመጫና ስልጣን ብቻ ሲሆን፣ በአንፃሩ እነዚህ H.R.6600 እና S.3199 ረቂቅ ህጎች በአሜሪካ መንግስት ደረጃ የቀረቡ በመሆናቸው የህጎቹ መፅደቅ ላይ ምንም አይነት መብትና ስልጣን አይኖራቸውም። 

ሁለተኛው እና አወዛጋቢ ጉዳይ የነበረው የS3199 ረቂቅ ህግ በቅርቡ ህግ ሆኖ ፀድቋል የሚል ነበር።

እነዚህ ሁለቱ ረቂቅ ህጎች ህግ ሆ 5 የተለያዩ ደረጃዎችን ማለፍ ይኖርባቸዋል። እነዚህም ለውጭ ጉዳዮች ኮሚቴ መተዋወቅ፣ በሴኔቱ መፅደቅ በመቀጠልም በምክር ቤቱ መፅደቅ ያለበት ሲሆን በመጨረሻም በፕሬዝዳንቱ ከፀደቀ በኋላ ህግ መሆን ይችላሉ። 

በሌላ መልኩ ረቂቁ በሴኔት አባል አማካኝነት የቀረበ ከሆነ በሴኔቱ የውጭ ግንኙነቶች ኮሚቴ አማካኝነት ድምፅ ተሰጥቶበት ወደ ሙሉ ሴኔት የሚተላለፍ ይሆናል። ነገር ግን ይህ ረቂቅ በተወካዮች ምክር ቤት አባል የቀረበ ከሆነ በውጭ ግንኙነቶች ኮሚቴ አማካኝነት ድምፅ ተሰጥቶበት ወደ ሙሉ የተወካዮች ምክር ቤት ይተላለፋል።

ከነዚህ በአሜሪካ ረቂቅ ህጎችን የማፅደቅ ሂደት አንፃር ስንመለከተው፣ S3199 ረቂቅ ህግ የቀረበው በሴናተር አማካኝነት ነው። በሴኔቱ የውጭ ግንኙነቶች ኮሚቴ አማካኝነት ረቂቁ መጋቢት 20 ቀን 2014 ዓ.ም በሴኔቱ ድምፅ እንዲሰጥበት ተላልፏል። ይህ ረቂቅ ህግ ሆኖ እንዲጸድቅ በሴኔቱ፣ በተወካዮች ምከር ቤት እና በአሜሪካው ፕሬዝደንት መፅደቅ አለበት። ይህ ረቂቅ ህግም ወደ ፕሬዝደንቱ ከማለፉ በፊት በሴኔቱ እና በተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት የሁለቱን ድምፅ ማግኘት አለበት።

በሌላ በኩል HR6600 የሚባለው ረቂቅ ህግ የተዘጋጀው በተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት ነው። ይህ ረቂቅም የካቲት 1 ቀን 2014 ዓ.ም በውጭ ጉዳይ ተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት ድምፅ ተሰቶበት ወደ አሜሪካ ተወካዮች ምክር ቤት ተላልፏል። በተመሳሳይ ሁኔታም ይህ ረቂቅ ህግ በተወካይ በሴናተሮች ፀድቆ በመጨረሻም በፕሬዝዳንቱ አማካኝነት ወደ ህግ መቀየር ይኖርበታል። 

ከዚህ መመልከት እንደምንችለው እነዚህ ሁለት ረቂቅ ህጎች እስካሁን ህግ ሆነው አልፀደቁም። በመሆኑም እነዚህ ረቂቅ ህጎች በሂደት ላይ ያሉ ሲሆኑ ህግ ሆነው እንዲፀድቁ ሶስት ሂደቶችን፤ ማለትም በሴኔቱ፣ በተወካዮች ምክር ቤት፣ እና በመጨረሻም በፕሬዝደንቱ ሊፀድቅ ይገባዋል።

Exit mobile version