ህወሓት ከፌደራል መንግስት ጋር ድርድር እንደማይፈልግ አስታውቋል?

አንድ የዩቲዩብ ቻናል በግንቦት ወር 2014 ዓ.ም ህወሓት ከኢትዮጵያ የፌደራል መንግስት ጋር ድርድር እንደማይፈልግ ገለፀ በሚል ርዕስ አንድ ቪድዮ አጋርቶ ነበር።

ሆኖም ቪድዮው ሲጫወት ያለው መልዕክት ህወሓት ያስቀመጣቸው አምስት የቅድመ ድርድር ነጥቦች እንዳሉ ይናገራል። የቪድዮው ርዕስ እና የሽፋን ምስል ህወሓት ድርድር እንደማይፈልግ የሚያስቀምጥ ቢሆንም የቪድዮው ይዘት ግን ህወሓት ለድርድሩ ያስቀመጣቸውን አምስት ቅድመ ሁኔታዎች ይናገራል። 

በዚህም ምክንያት ሀቅቼክ የዩቲዩብ ቪድዮው ያስተላለፈውን መልዕክት መርምሮ አሳሳች ብሎታል።

የፌደራል መንግስት እና ህወሓት እስካሁን ድረስ መፍትሄ ባላገኘ ጦርነት ውስጥ ይገኛሉ። 

በመጋቢት ወር 2014 ዓ.ም ሁለቱ ተዋጊ ሀይሎች የተኩስ አቁም ስምምነት [ለሰብዓዊ እርዳታ] ማድረጋቸው የሚታወስ ሲሆን ከዚያን በኋላ የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦቱ እየተሻሻለ መቷል።   

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፌደራል መንግስቱ እና በህወሓት ከፍተኛ አመራሮች መካከል ቀጥተኛ ንግግሮች እንደተደረጉ የሚያሳዩ ያልተረጋገጡ ሪፖርቶች ሲወጡ ቆይተዋል።

ይህ በእንዲህ እያለ የፌደራል መንግስቱ ከህወሓት ጋር ድርድሮችን ሊያደርግ እንደሆነ የሚያሳዩ የተለያዩ መረጃዎች እየወጡ ይገኛሉ።

ባለፈው ሳምንት ለ ሞንድ የተባለ የፈረንሳይ ጋዜጣ በድረ-ገጹ የኢትዮጵያ የፌደራል መንግስት ከህወሓት ጋር በግንቦት ወር መጨረሻ አካባቢ በታንዛኒያ አሩሻ ድርድር ሊያደርጉ እቅድ እንደተያዘ የሚገልፅ ፅሁፍ አስነብቧል። 

ይህ የፈረንሳይ ጋዜጣ ከተለያዩ የዲፕሎማት ምንጮቼ አግኝቼዋለው ባለው መረጃ መሰረት ህወሓት በምዕራብ ትግራይ ድንበር አካባቢ ላይ ያሉ ቦታዎች ላይ የሚያነሳውን የባለቤትነት ጥያቄ ትቶታል ብሎ ዘግቧል።   

ሆኖም ህወሓት ውዝግብ የተፈጠረባቸው የምዕራብ ትግራይ ቦታዎች ላይ ያለውን ጥያቄ ትቶታል የሚለው መረጃ ውሸት እንደሆነ አስታውቋል። 

ይህን ተከትሎ የህወሓት ሊቀመንበር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ለተለያዩ አካላት በፃፉት ግልፅ ደብዳቤ የሰላም ድርድር ለማድረግ ወደ ኬንያ ናይሮቢ የትግራይ ተወካዮችን እንደሚልኩ አስታውቋል። በአንፃሩ ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከፓርላማ ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሲሰጡ የፌደራሉ መንግስት ከህወሓት ጋር ለመደራደር ኮሚቴ እንዳዘጋጀም ተናግረዋል። 

በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድም ሆኑ ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ምስጢራዊ ውይይትም ሆነ ድርድር እንዳልተደረገ ገልፀዋል። 

ህወሓት በቅርብ በሰጠው መግለጫ በድርድሩ እንዲጠበቁለት የሚፈልጋቸውን ቅድመ ሁኔታዎች አስቀምጧል። ከነዚህም መካከል የምዕራብ ትግራይ ቦታዎች ጉዳይ፣ የሪፈረንደም ህዝበ ውሳኔ፣ የጦር ኃይሉን ይዞ መቀጠል እና በትግራይ ለተፈጠረው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተጠያቂነት የሚሉትን አስቀምጧል።

ሰኔ 9 ቀን 2014 ዓ.ም የህወሓት አመራር የሆኑት ፕሮፌሰር ክንደያ ገብረህይወት በትዊተር አካውንታቸው ህወሓት አልደራደርባቸውም የሚላቸውን አምስት ነጥቦች አስፍረዋል።         

ቪድዮው ይህን ሁኔታ ተገን በማድረግ የተለቀቀ ሲሆን በዚድዮው የተላለፈው መልዕክት ይዘት ህወሓት ለድርድር ስላስቀመጣቸው አምስት ነጥቦች ሆኖ ሳለ በቪድዮው ሽፋንና ርዕስ የተቀመጠው ምስልና ህወሓት ድርድር እንደማይፈልግ የሚገልፀው ርዕስ አሳሳች ያደርገዋል። 

በተጨማሪም ሀቅቼክ ህወሓት ከፌደራል መንግስት ጋር ለመደራደር የቅድመ ድርድር ነጥቦቹን እንዳስቀመጠ እንጂ ድርድር እንደማይፈልግ እንዳልገለፀ አጣርቷል። ስለዚህ ሀቅቼክ በዩቲዩብ ቪድዮው ሽፋኑ እና ርዕስ እንዲሁም በውስጥ ይዘቱ መልዕክት መካከል ያለውን ግንኙነት አጣርቶ አሳሳች ብሎታል።

የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ናቸው?

ሰኔ 2  ቀን 2014 ዓ.ም በአንድ የዩቲዩብ ቻናል ላይ የተላለፈ ቪድዮ ባሰራጨው መልዕክት የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እንደሆኑ ጠቅሶ ነበር። ቪድዮውም በመቀጠል ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ጋር ያላት ግንኙነት እየጠነከረ እንደመጣ ገልጾ በተቃራኒው ደግሞ ኤርትራ ከአሜሪካ ጋር ያላት ግንኙነት ደግሞ ይበልጥ እየሻከረ እንደመጣ ይናገራል።

ቪድዮው በትንታኔው በኤርትራው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና በአስመራ የአሜሪካ ኤምባሲ መካከል በፖለቲካ ፤ በሃይማኖት እና በአለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ አለመስማማት እና ጭቅጭቆች እንዳሉ በመናገር ይህም ለሁለቱ ሀገሮች ግንኙነት መሳሳት ይበልጥ አስተዋጽኦ እንዳደረገ ይናገራል።

አሜሪካ ከኤርትራ እና ኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት ይበልጡኑ እየሻከረ የመጣው በሰሜን ኢትዮጵያ ከተቀሰቀሰው ጦርነት ጋር ተያይዞ ሲሆን ኢትዮጵያ የታላቁ ህዳሴ ግድብ የመጀመርያ ሙሌት ማሳካቷን ተከትሎ አሜሪካ የምታደርገውን የገንዘብ እርዳታዎች ማቆምን ጨምሮ ማዕቀብ የመጣል ማስፈራሪያዎችን ስታሰማ ቆይታለች። ይህም ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት ለመሻከሩ እንደዋነኛ ምክንያት ይጠቀሳል። 

የፌደራሉ መንግስት ከህወሓት ጋር በነበረው ግጭት የአሜሪካ መግስት በክልሉ ለተፈጸሙት የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የኢትዮጵያን እና የኤርትራ መንግስት ተጠያቂ አድርጓል። 

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን የኤርትራ መንግስት ጦሩን ከትግራይ ክልል ሙሉ በሙሉ እንዲያስወጣ በተደጋጋሚ ሲጠይቁ የቆዩ ሲሆን በመጨረሻም የአሜሪካ መንግስት በኤርትራ እና በኤርትራ የጦር አመራሮች ላይ ማዕቀብ ጥሏል። 

የኤርትራ መንግስት በበኩሉ አሜሪካ ህወሓትን በማገዝ ለአፍሪካ ቀንድ እና ለቀጠናው አለመረጋጋት አስተዋጾ እያደረገች እንደሆነ ክስ አቅርቧል።  

የማነ ገብረመስቀል ከፍተኛ የኤርትራ መንግስት ባለስልጣን ሲሆኑ በማህበራዊ ሚድያ በተለይም በይፋዊ የትዊተር ገጻቸው ላይ በተደጋጋሚ የአሜሪካ መንግስት ህወሓትን እየረዳ እንደሆነና ይህ ደግሞ ይበልጥ ለቀጠናው አለመረጋጋት በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ እንደሚያግዝ በመናገር ትችት ሲሰነዝሩ ቆይተዋል።  

በአስመራ የአሜሪካ ኤምባሲ በበኩሉ በይፋዊ የፌስቡክ ገፁ አማካኝነት የኤርትራ መንግስት በኢትዮጵያ ትግራይ ክልል የሰብዓዊ መብት ጥሰት እየፈጸመ እንደሆነ በመግለፅ፣ የማነ ገብረመስቀል ሀሰተኛ መረጃን በመፈብረክ በማህበራዊ ሚድያ እያሰራጩ እንደሆነ ገልጿል።      

የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ሲሆኑ የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኦስማን ሳሌህ ናቸው። ኦስማን ሳሌህ ከኤርትራ ውጭ በሚኖራቸው ጉዞ የፕሬዝዳንቱ አማካሪ የማነ ገብረአብ አብረዋቸው ይታያሉ።     

የማነ ገብረመስቀል የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት የቀድሞው የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር የሆኑት አሊ አብዱ ሀገራቸውን ክደው መጥፋታቸው ከታወቀ በኋላ እኤአ በ2015 ነበር።
በዚህም መሰረት የማነ ገብረመስቀል የኤርትራ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር እንጂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እንዳልሆኑ በማረጋገጥ በዩቲዩብ ቻናሉ የተላለፈውን መረጃ ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል። 

ምስሉ በመንግስት ታጣቂዎች የወደመን የዘመነ ካሴን እናት ንብረት ያሳያል?

ከ150 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ግንቦት 23 ፤ 2014 ዓ.ም ላይ “ሰበር ዜና ‘ወያኔ ዘመነ ካሴ ኤርትራ በገባ ጊዜ እንዲህ የደካማ እናቱን ንብረት አላቃጠለም አልዘረፈም ነበር። ዛሬ የአብይ መንግስት በጭንቅ ጊዜ የራሱን ወንበር ብሎም ህዝብን የታደገውን የአርበኛ ዘመነ ካሴ እናት ልጅሽን አምጭ በማለት እንዲህ አውድሞታል።” የሚል ፅሁፍ በማያያዝ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። ዘመነ ካሴ የፋኖ መሪ እንደሆነ በተከታዎቹ ዘንድ የሚነገርለት ግለሰብ ነው።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከ 190 በላይ ግብረመልስ ሲያገኝ ከ65 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።  

ፋኖ ማለት ሀገር ለመጠበቅና ከጠላት ለመከላከል በበጎ ፈቃድኝነት የተሰባሰቡ የአማራ ወጣቶች የወል ስም ነው። በሰሜን ኢትዮጵያ የተነሳውን ጦርነት የትግራይ ኃይሎች በአጎራባች የአማራና የአፋር አካባቢዎች ባደረጉት መስፋፋት መንግስት ያቀረበውን የክተት ጥሪ ተቀብለው አያሌ የፋኖ አባላት ወደ ጦር ግንባር ዘምተዋል። በመንግስት በራሱ የታጠቁት የፋኖ አባላትም የህወሓት ኃይሎች የአማራን እና የአፋርን አካባቢዎችን ለቀው እስከወጡበት ጊዜ ድረስ ከሀገር መከላከያ ሰራዊት ጎን ተሰልፈው በውጊያ ተሳትፈዋል።

ታህሳስ 11 ቀን 2014 ዓ.ም የትግራይ ተዋጊ ሀይሎች በሰሜን ኢትዮጵያ ካሉ የትግራይ አካባቢዎች ለቀው መወጣታቸውን እና ከ13 ወራት ቆይታ በኋላ የተኩስ አቁም ስምምነትን ለማድረግ መወሰናቸውን አስታውቀዋል። 

መጋቢት 15 ቀን 2014 ዓ.ም የፌደራሉ መንግስት በትግራይ የተኩስ አቁም ስምምነት [ለሰብዓዊ እርዳታ ሲባል]አድርጓል።  በሰብዓዊ እርዳታ እጥረት ምክንያት ለሚጠፋው የሰው ልጅ ህይወትን ለመታደግ የፌደራሉ መንግስት ሰብዓዊ እርዳታን ግምት ውስጥ ያስገባ ተኩስ አቁም እንዲደረግ መወሰኑን አስታውቋል።

ይህን ተከትሎ ግንቦት 17 ቀን 2014 ዓ.ም የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በሰጠው መግለጫ “በአማራ ክልል ውስጥ ሁከት ፣ ብጥብጥ እና ስርዓት አልበኝነት በማስፈን ሕዝብ እንዳይረጋጋ እርስ በርሱ እንዲጋጭና አንድነቱን እንዲያጣ የሚያደርጉ ተግባራት በመፈፀም ራሳቸውን በአማራ ህዝብ ጉያ ውስጥ የወሸቁ ጠላቶችን ለማስቆም ጥረት እያደረገ እንደሆነ ገልፆ፣ እየተከናወነ ለሚገኘው የህግ የበላይነትን የማረጋገጥ መንግስታዊ ተግባር በዓላማው፣ በሂደቱም ሆነ በውጤቱ የሕዝብ እና የሀገር ደኅነነትን ለማረጋገጥ የታለመ መሆኑን በመገንዘብ መላው የአማራ ህዝብ ሕግ እና የሕግ የበላይነትን ለማስከበር ለሚደረገው ጥረት ሙሉ ውግንናውን በመስጠት ውስጣዊ አንድነቱን አጠናክሮ ሊያስቀጥል እንደሚገባ” ገልጿል።

ከዚህ በኋላ የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ አካውንቶች እና ድረ-ገፆች በፌደራል መንግስቱ እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ግጭት እንዳለ የሚያሳይ መረጃዎችን ሲያሰራጩ ነበር።  

እንደ ዋዜማ ሬድዮ ዘገባ ከሆነ የካቲት 27 ቀን 2014 ዓ.ም በምስራቅ ጎጃም ዞን ሞጣ ከተማ የፋኖ አመራር በመንግስት መታሰሩን ተከትሎ በፋኖ ታጣቂዎች እና በፊደራሉ መንግስት መካከል ግጭት ተከስቶ ነበር።   

የክልሉ መንግስት በበኩሉ ሁኔታውን የህግ ማስከበር ሂደት ነው በማለት ምላሽ የሰጠ ሲሆን ሁኔታው ክልሉን ለመረበሽ በሚንቀሳቀሱ ሀይሎች እንደተፈጠረ ገልጿል። የአማራ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ይልቃል ከፍያለ “መንግስት ፋኖን ማጥቃትም ሆነ ትጥቅ የማስፈታት አላማ እንደሌለው በማስረዳት ዘመቻው ትኩረት ያደረገው በክልሉ በህገወጥ የመሳርያ ዝውውር በግድያ እና በዝርፍያ የሚሳተፉ ሀይሎችን እንደሆነ ገልፀው ነበር። 

ይህ በእንዲህ እያለ መንግስት የፌደራል እና የክልል የፀጥታ አካላት በፋኖ አመራሮች ቤት በመግባት ማሰር እንደጀመሩ የሚናገሩ የተለያዩ ሪፖርቶች ወጥተዋል።    

ግንቦት 15 ቀን 2014 ዓ.ም My views on news የተባለ ድረ-ገፅ “ፋኖ ዘመነ ካሴ የፌደራል መንግስቱን አስጠነቀቀ” በሚል ርዕስ አንድ ፅሁፍ አስነብቦ ነበር።

የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶችም የፋኖ ዘመነ ካሴ ቤተሰብ ቤቶች እና ንብረቶች እንደወደሙ እና እንደተቃጠሉ ሲገልፁ ቆይተዋል። አንድ ከ180 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ “የዘመነ ካሴ ወንድም ንብረት ካሴ የ85 አመት እድሜ ያላቸው እናታቸው ቤትና ንብረት በመንግስት ታጣቂዎች እንደወደመ ገልጿል” በማለት መረጃውን አጋርቶ ነበር።   

ሀቅቼክ ያገኘው የፌስቡክ ፖስትም ይህን ሁኔታ ተገን በማድረግ የተለጠፈ ነበር። 

ሀቅቼክ ምስሉን ለማጣራት ባደረገው ጥረት ምስሉን ከ3 የተለያዩ ምስሎች ጋር ቀደም ባለ ጊዜ ተጋርቶ አግኝቶታል። ምስሉ ከዚህ ቀደም ጥር 15 ቀን ከ13ሺ በላይ ተከታይ ባለው የትዊተር አካውንት ላይ “ከአባይ ተሻግረው የመጡ ታጣቂዎች በሆሮ ጉድሩ ዞን የኦሮሞ ገበሬ ቤቶችን አቃጥለዋል” በሚል ርዕስ ተለጥፎ ነበር። 

የፋኖ ዘመነ ካሴ እናት ቤት እንደተቃጠለ የሚያሳዩ የተለያዩ መረጃዎች ቢኖሩም ይህ የፌስቡክ ፔጅ የተጠቀመው ምስል መረጃው በፌስቡክ ገፁ ከተጋራበት ጊዜ እጅግ ቀደም ብሎ የተላለፈና የተባለውን ዜና የማይደግፍና የተሳሳተ እንደሆነ ታውቋል።
ስለዚህ ሀቅቼክ መረጃውን ለመደገፍ ጥቅም ላይ የዋለውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።      

ሀሰት፡ ምስሉ በቅርቡ ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከመራራ ጉዲና ጋር መገናኘታቸውን አያሳይም

ከ25ሺ በላይ ተከታይ ያለው የትዊተር አካውንት ግንቦት 25 ቀን 2014 ዓ.ም ላይ “ኦባሳንጆ ከታላቁ የፖለቲካ ልሂቅ ፕርፌሰር መራራ ጉዲና ጋርም ስለ ሰላም መክረዋል!” በሚል የፅሁፍ መግለጫ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የትዊተር ፖስቱ ከ150 በላይ ግብረ መልሶችን ሲያገኝ ከ35 ጊዜ በላይ ሪትዊት ተደርጓል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

በህወሓት እና በፌደራል መንግስት መካከል የተቀሰቀሰው ጦርነት እስካሁን ድረስ ያልተፈታ ችግር ሆኗል። 

ከጥቂት ወራት በፊት ለሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት በሚል በፌደራሉ መንግስት የቀረበው የተኩስ አቁም ስምምነት በህወሓት ዘንድ ተቀባይነትን አግኝቶ የነበረ ሲሆን ይህ ስምምነት ለሰላም ንግግር እና ግጭቱን ለማቆም ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር ተገምቶ ነበር። 

የቀድሞ የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት የነበሩት ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ነሀሴ 20 ቀን 2013 ዓ.ም የምስራቅ አፍሪካ ከፍተኛ ተወካይ ሆነው መሾማቸውን የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበር የሆኑት ሙሳ ፋኪ አሳውቀዋል። የምስራቅ አፍሪካ ከፍተኛ ተወካዩም በቀጠናው ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት ለማምጣት የሚሰሩ ይሆናል።

ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከመንግስት ሀላፊዎችና ከህወሓት አመራሮች ጋር ሰላማዊ መፍትሄ ለማምጣት በተደጋጋሚ ተገናኝተዋል። በጦርነት ውስጥ የሚገኙት ሁለቱም አካላት ጦርነት እንዲያቆሙና ወደ ድርድር እንዲመጡ ሀላፊነት ወስደው እየሰሩ ይገኛሉ። 

ግንቦት 23 ቀን 2014 ዓ.ም በአፍሪካ ቀንድ የአፍሪካ ኅብረት ልዩ መልዕክተኛ ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከህወሓት ሊቀመንበር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ጋር በመቀሌ ከተማ ተገኝተው ተነጋግረዋል። ከሁለት ቀናት በኋላም ለስራ ጉብኝት ከጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ ጋር ባሌ ሮቤ ተገኝተው ጉብኝት አድርገዋል። 

የትዊተር ፖስቱም ይህን አውድ ታሳቢ በማድረግ የተጋራ ነበር። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት ለማጣራት ባደረገው ምርመራ ምስሉ ከዚህ ቀደም የነበረና የቆየ  ሆኖ ያገኘው ሲሆን “የአፍሪካ ህብረት ምርጫ ታዛቢ ቡድን የበላይ ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ ከኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሊቀ መንበር ዶ/ር መራራ ጋር ተገናኝተዋል።”በሚል በአፍሪካ ህብረት ይፋዊ ድረ ገጽ ላይ በሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ተጋርቶ አግኝቶታል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ የቲዉተር ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

የተቀናበረ፡ ምስሉ በትግራይ የተቀሰቀሰ አመፅን አያሳይም

ከ1100 በላይ ተከታይ ያለው የትዊተር አካውንት ግንቦት 16 ፤ 2014 ዓ.ም ላይ “ሰበር መረጃ’ በትግራይ ክልል አመፅ ተቀስቅሷል ፤ የትግራይ ህዝብ አብይ አህመድ ይምራን እያለ ነው” የሚል ፅሁፍ አያይዞ ሶስት ምስሎችን አጋርቶ ነበር።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የትዊተር ፖስቱ ከ80 በላይ ግብረ መልሶችን ሲያገኝ ከ30 ጊዜ በላይ ሪትዊት ተደርጓል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሎቹን መርምሮ የተቀናበረ ብሏቸዋል።

በህወሓት እና በፌደራል መንግስቱ መካከል የተከሰተው ግጭት እስካሁን ድረስ መፍትሄ ያላገኘ ጉዳይ ሆኖ ቆይቷል።

ህወሓት ጦርነቱ እንዲያበቃ የተኛውንም አይነት የዲፕሎማሲያዊ መንገዶችን እንደሚከተል እና ያ የማይሆን ከሆነ ግን መልሶ ወደ ጦርነቱ ሊገባ እንደሚችል ተናግሯል። ህወሓት የሰብዓዊ እና የመድሃኒት እርዳታ ወደትግራይ ክልል እንዳይገባ የፌደራል እና የክልል መንግስታት እያገዱ ነው በማለት በተደጋጋሚ  ክስ ሲያቀርብ ቆይቷል።   

ግንቦት 12 ፤ 2014 ዓ.ም ህወሓት እንዳስታወቀው የትግራይ መንግስት የፖለቲካ ልዩነትን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ያለውን ቁርጠኛነት ለማሳየት ለአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ለሆኑት የቀድሞ የናይጄርያ ፕሬዝዳንት ኦሊሴጎን ኦባሳንጆ በገባው ቃል መሰረት 4208 የሚሆኑ የጦር እስረኞችን የፈታ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ 401 የሚሆኑት ሴቶች እንደሆኑ በመግለጫው አስታውቋል።

ጥር 5 ቀን 2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኢታዦማር ሹም የሆኑት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ “የትግራይ ህዝብ ለህወሓት ሲል ከዚህ በላይ መሞት የለበትም። በሺዎች የሚቆጠር ህይወት ጠፍቷል። የትግራይ ህዝብ ህወሓትን እምቢ ማለት አለበት።” ብለው ነበር። 

የትዊተር ፖስቱም ይህን አውድ ታሳቢ በማድረግ የተጋራ ነበር። 

ሀቅቼክ ምስሎቹን ለማጣራት ባደረገው ጥረት ሁለቱ ምስሎችDW አማርኛ የፌስቡክ ገፅ ላይ መስከረም 22 ቀን 2011 ዓ.ም በተጋራ ፖስት ላይ “ለደህንነታችን እንሰጋለን ያሉ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ሌሎች ተሳታፊዎች ዛሬ በመቐለ ሰልፍ አካሄዱ። ሰልፈኞቹ የደህንነት ስጋት ባለባቸው አካባቢዎች መማር እንደሚሰጉ በመግለፅ መንግስት መፍትሄ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።” በሚል ፅሁፍ ስር አግኝቶታል።

በሰልፉ ላይ “የተጋሩ ተማሪዎች ህይወት ያሳስበኛል፣ ዋስትና ወደሌለው ቦታ ልጆቻችን አንልክም፣ ተማሪዎች ትርጉም የሌለው መስዋእት መክፈል የለባቸውም፣ የክልል እና ፌደራል መንግስታት መፍትሄ ይስጡን” የሚሉ መፈክሮች ተስተጋብተዋል።

ምስል አንድ 

ምስል ሁለት

ሶስተኛው ምስል ሰኔ 20 ቀን 2010 ዓ.ም borkena.com በተባለ ድረ-ገፅ ላይ “Fresh ethnic-based violence in Asossa left at least eight people dead.” በሚል ፅሁፍ ስር አግኝቶታል። 

የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ምንጮችን በመጥቀስ የተፃፈው ይህ ዜና “የበርታ ተወላጅ ነን የሚሉ ወጣቶች በዚያ አካባቢ የሚኖሩ ሌሎች የአማራ እና ኦሮሞ ነዋሪዎች የሚያንቀሳቅሷቸው ቢዝነስ ተቋማት ላይ በተቀናጀ መልኩ ጥቃት ሰንዝረዋል። ይህን ተከትሎም የአማራ ተወላጆች የመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ እንዳደረጉ ቢሰማም ከበርታ ማህበረሰብ የተጎዳ ይኑር አይኑር የተጣራ መረጃ አልተገኘም” በማለት ያስነብባል።  

ምስል ሶስት       

የመጀመርያ ሁለቱ ምስሎች በትግራይ የነበረን ህዝባዊ ሰልፍ የሚያሳዩ ቢሆንም መረጃውን ለመደገፍ ምስሉ ተቀናብሯል። ከዚያ በተጨማሪ ሶስተኛው ምስል ደግሞ ከትግራይ ክልል እንዳልሆነ ተረጋግጧል።
ስለዚህ ሀቅቼክ ምስሎቹን መርምሮ እና አጣርቶ የተቀናበሩ እንደሆኑ አረጋግጧል።

ምስሎቹ ኢትዮጵያ የታጠቀቻቸውን C-130 ሄርኩሊዝ የጦር አውሮፕላኖችን ያሳያል?

አንድ የፌስቡክ ፖስት ግንቦት 7 ፤ 2014 ዓ.ም ኢትዮጵያ የታጠቀቻቸው C-130 ሄርኩሊዝ ጀቶች የሚል ፅሁፍን አያይዞ አምስት ምስሎችን አጋርቶ ነበር።

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ከ44 ጊዜ በላይ ሲጋራ ከ500 በላይ ግብረ መልሶችንም ማግኘት ችሎ ነበር።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን አጣርቶ መረጃውን በከፊል ሀሰት ብሎታል። 

በህወሓት እና በፌደራል መንግስቱ መካከል የተቀሰቀሰው ጦርነት እስካሁን ድረስ ያልተፈታ ችግር ሆኗል። 

ከጥቂት ወራት በፊት ለሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት በሚል በፌደራሉ መንግስት የቀረበውን የተኩስ አቁም ስምምነት በህወሓት ዘንድ ተቀባይነትን አግኝቶ የነበረ ሲሆን ይህ ስምምነት ለሰላም ንግግር እና ግጭቱን ለማቆም ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር ተገምቶ ነበር። 

የተኩስ አቁም ስምምነቱ ከታወጀ በኋላ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እና በህወሓት አመራር በሆኑት ደብረፅዮን ገብረሚካኤል መካከል የቀጥታ የስልክ ንግግር (ውይይት) ተደርጓል የሚሉ ያልተረጋገጡ ሪፖርቶች ሲወጡ ነበር።

በዩትዩብ በተለቀቀ አንድ የድምፅ መረጃ መሰረት የህወሓት ከፍተኛ የጦር አመራር የሆኑ አንድ ሰው ከታደሰ ወረደ ጋር በመሆን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኤታማጆር ሹም የሆኑት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላን በሞሪሽየስ አግኝተው እንዳወሯቸው ገልፀዋል። 

ነገር ግን ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከህወሓት አመራሮች ጋር ተገናኝተው ስለ መወያየታቸው የሚሰራጨውን መረጃ ሀሰት እና መሰረተ ቢስ መሆኑን ተናግረዋል።

ህወሓት በመግለጫዎቹ ግጭቱን ለማቆም ሰላማዊው መንገድ የማይሳካ ከሆነ በጦርነቱ እንደሚቀጥል ገልጿል

ህወሓት በተለያዩ ጊዜያቶች የፌደራል መንግስቱ እና የክልል ባለስልጣናት እርዳታ ወደ ትግራይ ክልል እንዳይገባ እየከለከሉ ነው በሚል በተደጋጋሚ የተለያየ ክስ ሲያቀርብ የቆየ ሲሆን አሁንም ወደ ትግራይ ክልል የደረሰው እርዳታ በቂ አለመሆኑን ተናግሯል።

ከሳምንታት በፊትም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትን በሁመራ በአካል ተገኝተው ጎብኝተዋል። 

ይህ በእንዲህ እንዳለ በአንፃሩ ህወሓት በተለያዩ የትግራይ ከተሞች የህዝብ ለህዝብ ውይይት አካሂዶ የነበረ ሲሆን የህወሓት አመራር የሆኑት ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ፤ ፈትለወርቅ ዘውዴ ፤ ጌታቸው ረዳ እና አለም ገብረዋህድ ተገኝተው ውይይቱን መርተውታል።

ግንቦት 2 ቀን 2014 ዓ.ም በተካሄደው በዚህ የህዝብ ውይይት ደብረጽዮን ገብረሚካኤል “ለሰላም ያደረገነው ጥረት ስላልተሳካ አሁን ለመጨረሻው የጦርነት ምዕራፍ እንድትዘጋጁ” በማለት ለህዝቡ ጥሪ አቅርበዋል።

በቅርቡ አዳዲስ የወረራ እና የግጭት ሪፖርቶች እየወጡ የሚገኙ ሲሆን ይህም ሁኔታ ሀገሪቷ በድጋሚ ሙሉ በሙሉ ወደ ጦርነት እንዳትገባ ስጋትን ፈጥሯል።

ከዚህ ጋር በተያያዘም ህወሓት የጦርነት ነጋሪት እየጎሰመ ነው በማለት ህወሓት ወደሌላ ጦርነት እንዳይገባ  የአውሮፓ ህብረት ጫና እንዲያደርግበት የፈደራሉ መንግስት ጠይቋል።  

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ኢትዮጵያ ያሏትን የC-130 ሄርኩሊዝ አውሮፕላን ጀቶችን ያሳያል በማለት አምስት ምስሎችን አጋርቷል። 

የአሜሪካ መንግስት ግንቦት 29 ፤ 2010 ዓ.ም ላይ C-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላኖችን ሀገሪቱ ለምታካሄደው የሰላም ማስከበር ተልዕኮ እንዲያግዛት ለኢትዮጵያ አስረክቧል። 

የፌስቡክ ፖስቱ ከተጠቀመባቸው ምስሎች መካከል አንዱ ይህ አሜሪካ ለኢትዮጵያ የለገሰችው የጦር አውሮፕላን ይገኝበታል። ይሁን እንጂ ከአምስቱ ምስሎች ቀሪዎቹ አራቱ የተወሰዱት ከሌላ እትሞች ሲሆን ኢትዮጵያ የታጠቀችውን C-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላኖችን አያሳዩም።   

ምስል አንድ

ሰኔ 24 ቀን 2006 ዓ.ም በአንድ የዩቲዩብ ቻናል ላይ የተለቀቀው ይህ ቪድዮ የAirbus A400M የጦር አውሮፕላን ያሳያል። 

ምስል ሁለት 

ምስሉ በየካቲት 21 ቀን 2010 ዓ.ም በአሜሪካ የመከላከያ ዲፓርትመንት ትዊተር ገፅ ላይ ከተለቀቀ ቪድዮ ላይ ተቆርጦ የተወሰደ ሲሆን ምስሉ የሚያሳየው በቅፅል ስሙ “የሞት መልዓክ” ወይም “Angel of Death” የተሰኘውን AC-130 የተባለ ሄርኩሊዝ የጦር አውሮፕላን ነው። 

ምስል ሶስት 

ምስሉ የተወሰደው በአሜሪካ የመከላከያ ዲፓርትመንት በኩል ከተለቀቀ ቪድዮ ሲሆን ከአሜሪካ መንግስት ለኢትዮጵያ የተሰጠውን የC-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላን ላይ ከአሜሪካ የመጡ ባለሙያዎች ለኢትዮጵያውያን አብራሪዎች እና ቴክኒሽያኖች ትምህርት እየሰጡ እንደሆነ የሚያሳይ ምስል ነው።

ምስል አራት 

ምስሉ በግንቦት 5 ቀን 2014 ዓ.ም በአንድ የዩቲዩብ ቻናል ላይ ከተለቀቀ ቪድዮ ላይ በመውሰድ የተጋራ ሲሆን ይህ የዩቲዩብ ቻናልም መስከረም 5 ቀን 2013 ዓ.ም ላይ ከተጋራ ሌላ የዩቲዩብ ቪድዮ ላይ የተወሰደ ነው። ቪድዮውም የአሜሪካውን C-130 ሄርኩለስ የጦር አውሮፕላንን ያሳያል። 

ምስል አምስት

እንደ ምስል አራት ሁሉ ምስል አምስትም ግንቦት 5 ቀን 2014 ዓ.ም ከተለቀቀ የዩቲዩብ ቪድዮ ላይ የተወሰደ ሲሆን ይህ የ ዩቲዩብ ቻናልም መስከረም 5 ቀን 2013 ዓ.ም ከተለቀቀ ሌላ የዩቲዩብ ቪድዮ ላይ የወሰደ ሲሆን ቪድዮው የአሜሪካውን C-130 ሄርኩሊዝ የጦር አውሮፕላን ጥንካሬን የሚያሳይ ነው።

ይሁን እንጂ የፌስቡክ ፓስቱን ለመደገፍ ከተጋሩት  ከአምስቱ ምስሎች መካከል አንዱ ምስል ብቻ የኢትዮጵያን C-130 የሚያሳይ ሲሆን የቀሩት አራት ምስሎችይህን አውሮፕላን አያሳዩም።
ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱን በከፊል ሀሰት ብሎታል።   

ሀሰት ፡ ምስሉ የኦነግ ሸኔ ጦርን የተቀላቀሉ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን አያሳይም

ከ 70 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ግንቦት 6 ቀን 2014 ዓ.ም ላይ “በርከት ያሉ የመከላከያ ሰራዊት አባላት የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊትን መቀላቀላቸውን ሰምተናል” በሚል ፅሁፍ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።  

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቡክ ፖስቱ ከ200 በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ20 ጊዜ በላይ መጋራት ችሏል። 

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል አጣርቶ ሀሰት ብሎታል። 

በፌደራል መንግስቱ ዘንድ ኦነግ ሸኔ እየተባለ የሚጠራው እና እራሱን ደግሞ የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት ብሎ የሚጠራው ወታደራዊ ቡድን እስከ ሚያዝያ 23 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ወታደራዊ ክንፍ ነበር። ከዚያ በኋላ እራሱን ከኦሮሞ ነፃነት ግንባር ተለይቶ የትጥቅ ትግልን አማራጩ አድርጓል። 

የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ፓርቲ ሚያዝያ 1 ቀን 2014 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ የፌዴራሉ መንግስት ከኦነግ ሸኔ ጦር ጋር እያደረገ ያለውን ግጭት በሰላማዊ መንገድ በመፍታት ሁለቱ ሀይሎች ወደ ሰላማዊው የፖለቲካ ምህዳር እንዲገቡ ጠይቋል። በተጨማሪም መንግስት ለትግራይ ክልል የሰጠውን የሰላም አማራጭ [ተኩስ አቁም] ዕድል ኦነግ ሸኔንም በተመለከተ እንዲተገበረው ጠይቋል።

ቅዳሜ መጋቢት 24 ቀን 2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት የደቡብ እዝ አመራር የሆኑት ኮሎኔል ግርማ አየለ በቡድኑ ላይ የማያዳግም እርምጃ እየተወሰደ እንዳለ ገልፀው ነበር። የፌዴራሉ መንግስት ከክልል ሀይሎች ጋር ባደረገው ጥምረት የተቀናጀ ጥቃት በቡድኑ ላይ እያደረሰ እንደሆነ ኮሎኔሉ ገልፀው ቡድኑ ዘርፏቸው የነበሩ መሳሪያዎች ጥይቶች እና የመድሃኒት አቅርቦቶች እንደተማረኩም አስታውቀዋል።  

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ባለፉት ሳምንታት በኦሮሚያ ክልል  በሰላማዊ ዜጎች ላይ የደረሱ የተለያዩ የጅምላ ጭፍጨፋዎች እና የአየር ጥቃቶች እንዳሉ የሚያሳዩ የተለያዩ ሪፖርቶች ወጥተዋል። 

የመከላከያ ሰራዊት፤ የፌደራል ፖሊስ አባላት እና ሪፐብሊካን ጋርዶች በዘር በመከፋፈል ወደ ኦነግ ሸኔ እየተቀላቀሉ ነው የሚል የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶችም ተስተውለዋል።

ወደ ኦነግ ሸኔ የተቀላቀሉ የሪፐብሊካን ጋርድ አባላት ሊንክ   

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በዘር እየተከፋፈሉ ኦነግ ሸኔን እየተቀላቀሉ ነው ሊንክ 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህንን አጋጣሚ እና ሁኔታን መሰረት አድርጎ የተጋራ ነው።    

ሀቅቼክ ምስሉን ለማጣራት ጥረት ያደረገ ሲሆን ምስሉ ከዚህ በፊት ጥቅምት 21 ቀን 2014 ዓ.ም ከ140 ሺህ በላይ ተከታይ ባለው የፌስቡክ ገፅ ላይ የተጋራ ሲሆን ከፎቶው ጋር የተያያዘው መግለጫ ፅሁፍም እንዲህ ይነበበባል “የአብይ አህመድ መከላከያ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ፈርሷል። በዚህም ከደሴ የተረፈው ኮምቦልቻ ከተማን ለቆ ወደ ከሚሴ ቢሄድም ከሚሴ ላይ ትጥቁን ለአካባቢው ህዝብ አስረክቦ ወደ መሀል ሀገር ለመሄድ፣ ማምለጫ መኪና አጥተው እየተንገላቱ ነው። እንደ አጋጣሚ ገንዘብ ያላቸው በኮንትራት መኪና ለሊት ወጥተው አምልጠዋል።” 

የፌደራል ሀይሎች መንግስትን ክደው ወደ ኦነግ ሸኔ እየተቀላቀሉ ነው የሚሉ የተለያዩ የማህበራዊ ሚድያ ፖስቶች ቢኖሩም የፌስቡክ ገፁ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመው ምስል የተሳሳተና የቀረበውን ሪፖርት የማያሳይ መሆኑ ታውቋል።

ይህም በመሆኑ ሀቅቼክ ምስሉን አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።  

ሀሰት: ምስሉ ደምቢዶሎ ዩኒቨርስቲን አያሳይም

ከ500 ሺህ በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ ሚያዚያ 28 ቀን፣ “የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት ደምቢ ዶሎን መቆጣጠሩን ገለፀ” የሚል የፅሁፍ መግለጫ ያለው አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። መረጃውንም ለመደገፍ ከተቀመጡ ሦስት ምስሎች መሀል በአንደኛው ላይ “ደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ” በሚል በቀይ ቀለም ተፅፎበታል።

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ3ሺ በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ 950 ጊዜ በላይ ተጋርቷል።

ቢሆንም ሀቅቼክ በቀይ ቀለም “ደምቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቲ” ተብሎ የተፃፈበትን ምስል ለማጣራት ባደረገው ምርመራ ምስሉ ደምቢዶሎ ዩንቨርሲቲን እንደማያሳይ አረጋግጧል።

ይህም በመሆኑ ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት አጣርቶ ሀሰት ብሎታል።

የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት፣ የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦነግ) ወታደራዊ ክንፍ የነበረ ሲሆን ሚያዚያ 23 ፣ 2013 ዓ.ም ለሁለት ተከፍሏል። በኢትዮጲያ መንግስት “ኦነግ ሸኔ” እየተባለ የሚጠራው የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት በፓርላማ በአሸባሪነት ተፈርጇል።

የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት ከመንግስት ጋር በጦርነት ላይ ከሚገኘው ሕወሃት ጋር ጥምረት መፍጠሩን በነሀሴ 2012 አሳውቋል። 

የመንግስት ኮምኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር አቶ ለገሰ ቱሉ መጋቢት 24 ቀን 2014 ዓ.ም የኦሮሚያ ክልልና የፌደራል የፀጥታ ኃይሎች በተቀናጀና ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ በኦነግ ሸኔ ላይ እርምጃ እየወሰዱ እንደሚገኙ ገልፀዋል

በተጨማሪም መንግስት በምዕራብ ወለጋ በሚገኙት በነቀምት፣ በደምቢዶሎ እና በሌሎችም አከባቢዎች በኦነግ ሸኔ ላይ ጥቃት እየፈፀመ እንደሚገኝ የኮምኒኬሽን ሚኒስትሩ ገልፀዋል። 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህን ሁኔታ እና ወቅት በመጠቀም መረጃውን እንዲደግፍለት የኦሮሞ ነፃ አውጪ ሰራዊት በምዕራብ ወለጋ የሚገኘውን ደምቢዶሎ ከተማን መቆጣጠሩን ለማሳየት “ደምቢዶሎ ዩኒቨርስቲ” የሚል በምስል ላይ የተፃፈ ፅሁፍ አጋርቷል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት ለማጣራት ባደረገው ምርመራ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ በር የሚያሳየውን ምስል ከዚህ ቀደም ታህሳስ 12 ቀን 2010 ዓ.ም ላይ በቢቢሲ አማርኛ ዜና ‘በወለጋ ዩኒቨርሲቲ ሁለት ተማሪዎች ሞቱ’ በሚል ተጋርቶ አግኝቶታል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

ሀሰት ፡ ምስሉ በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያ ሰራዊት የተማረኩ የጣልያን ወታደሮችን አያሳይም

ሚያዝያ 25 ቀን 2014 ዓ.ም አንድ የፌስቡክ ገፅ “በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያ ጦር የተማረኩ የጣልያን ወታደሮች” በሚል የፅሁፍ መግለጫ አንድ ምስል አጋርቶ ነበር። 

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ300 ጊዜ በላይ መጋራት ሲችል ከ አንድ ሺህ በላይ ግብረ መልስ ማግኘትም ችሏል። ሀቅቼክ ይህ ምስል የተካተተበት በመረጃ ማጣራት ፅሁፉን የዛሬ አመት ለንባብ አብቅቶ ነበር።

ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ ያቀረበውን መረጃ ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል። 

የአድዋ ጦርነት 1896 እአአ በጣልያን ወራሪ ኃይል እና በአጼ ሚኒሊክ በሚመራው በኢትዮጵያ ጦር መካከል የተደረገ ጦርነት ሲሆን በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል በሚገኘው አድዋ ከተማ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ እንደተከናወነ ታሪክ ያሳያል። 

ወራሪው የጣልያን ጦር በኤርትራ በኩል ወደ ደቡብ አቅጣጫ ተጉዞ ኢትዮጵያን ለመቆጣጠር ጥረት አድርጎ የነበረ ሲሆን በጀነራል ኦሬስት ባራቴሪ የሚመራውና ዘመናዊ መሳርያን የታጠቀው የጣልያን ጦር በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያውያን ሽንፈት ገጥሞታል። በጦርነቱም በቁጥር የበዙ የጣልያን ወታደሮችና ከጣልያኖች ጋር ሲሰሩ የነበሩ ቅጥረኛ ወታደሮች አብዛኞቹ ሲገደሉ የቀሩት ተማርከዋል።   

ይህ የፌስቡክ ፖስት የተጋራው 81ኛው የኢትዮጵያ አርበኞች ቀን ከሚከበርበት ከሚያዝያ 27 ቀን 2014 ዓ.ም ሁለት ቀናት በፊት ነበር። በየአመቱ ሚያዝያ 27 ቀን የሚከበረው የአርበኞች ቀን መታሰቢያነቱ ሚያዝያ 27 ፤ 1933 ዓ.ም የጣልያን ወረራ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ያበቃበትን እና የንጉስ አጼ ስላሴን ከስደት ወደ ሀገራቸው መመለሳቸውን ለመዘከር የሚከበር ብሄራዊ በዓል ነው። 

ይህ የፌስቡክ ፖስትም ይህን ወቅት እና ሁኔታ በመጠቀም በአድዋ ጦርነት በኢትዮጵያ ሰራዊት የተማረኩ የጣልያን ወታደሮች በማለት ምስሉን ሊያጋራ ችሏል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ምስሉ በጦርነቱ ወቅት በኢትዮጵያ ወታደሮች የተማረኩ የጣልያን ወታደሮችን እንደማያሳይ አረጋግጧል።

ምስሉ የተወሰደው በሚያዝያ ወር 1937 ዓ.ም አካባቢ በነበረ ሁነት ሲሆን ኢንሳይክሎፒድያን ጨምሮ የተለያዩ ድረ-ገፆች ላይ ይገኛል።

ምስሉ በመጀመሪያ በቀረበበት ድረ-ገፅ እንደተገለፀው ምስሉ የሚያሳየው በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወቅት በጀርመን ጫካዎች ውስጥ የተማረኩ የናዚ ወታደሮችን ሲሆን የአሜሪካ የ12ኛ ክፍለ ጦር አባል የሆነ አንድ ወታደር እነዚህን የጀርመን ወታደሮች ሲጠብቃቸው የሚያሳይ ምስል እንደሆነ ይናገራል። 

ስለዚህ ሀቅቼክ የፌስቡክ ገፁ የተጠቀመውን ምስል መርምሮ ሀሰት ብሎታል።       

ሀሰት: ምስሉ በቅርቡ በህገወጥ የመሬት ወረራ ተወስዶ ለእርሻ ስራ የዋለ ቦታን አያሳይም

ከ 2 ሚሊዮን በላይ ተከታይ ያለው የፌስቡክ ገፅ መጋቢት 26 ቀን፣ “በህገወጥ የሚወረረው ቦታ እያለቀ ሲመጣ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የወጣቶች ማዘውተርያ የሆኑ ሜዳዎችን ለገበሬ በሚል ሰበብ ለልዩ ጥቅመኞች እየታደለ ነው። ይሄ ሀያት አካባቢ ልጆች ሲጫወቱበት የነበረ ሜዳ ነው በንጋታው ሲመጡ ታርሶ ጠብቋቸዋል” የሚል የፅሁፍ መግለጫ ያለው አንድ ምስል አጋርቶ ነበር።  

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የፌስቡክ ፖስት ከ1500 በላይ ግብረ መልስ ሲያገኝ ከ 156 ጊዜ በላይ ተጋርቷል።

ነገር ግን የፌስቡክ ፖስቱ ፅሁፉን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል ትክክለኛነት አጣርቶ ሀሰት ሀቅቼክ ብሎታል።    

የቅርብ መረጃዎች በአዲስ አበባ ከተማ መጠነ ሰፊ ህገወጥ የመሬት ወረራ እንዳለ የጠቆሙ ሲሆን፤ በቃሊቲ ፣ በለሚ ኩራ፣ በቦሌ እና በንፋስ ስልክ ክፍለ ከተሞች ላይ በስፋት መስተዋሉንም ገልፀዋል።

በአንድ ተቃዋሚ ፓርቲ በጉዳዩ ላይ የሰራው ጥናት ግኝቶች መሰረት የመሬት ወረራው ግንባር ቀደም ተሳታፊዎች “ቦታዎቹ ከዚህ ቀደም የቤተሰቦቻችን መሬቶች በመሆናቸው በቂ ካሳ ሳይከፈለን ከቦታችን ተነስተናል” የሚሉ ግለሰቦች እና ወረራ በተፈፀመባቸው ቦታዎች አካባቢ የሚገኙ የክፍለ ከተማና የወረዳ ኃላፊዎችና ፈፃሚዎች አንደሆኑ በመጥቀስ ፣ “ጉዳዩን በማፋጠን ሕገ-ወጥ ደላላዎችም ተሳታፊዎች ነበሩ” ብሏል።

በፌስቡክ ገፁ የቀረበው መረጃም ይህን ሁኔታ መሰረት አድርጎ የቀረበ ነው። 

ሀቅቼክ የምስሉን ትክክለኛነት ለማጣራት ጥረት ያደረገ ሲሆን ምስሉ ከዚህ ቀደም ግንቦት 21 ቀን 2011 ዓ.ም “አዲስ አበባ የእግር ኳስ ሜዳዎቿ በ “ባለ ጊዜ ነን” ባዮች ወደ እርሻ ማሳነት እየተቀየሩ ነው” በሚል ርዕስ የወጣ ፅሁፍ አካል ሆኖ አግኝቶታል። 

ሀቅቼክ የፌስቡክ ፖስቱ ፅሁፉን ለመደገፍ የተጠቀመው ምስል የቆየ እና ከመረጃው ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የሌለው መሆኑን አረጋግጧል።

ይህም በመሆኑ የፌስቡክ ፖስቱ መረጃውን ለመደገፍ የተጠቀመውን ምስል አጣርቶ ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል።  

Exit mobile version