ከዚህ በፊት ሃቅ ቼክ ባስነበበው ጽሁፍ ፣ በአንዳንድ የቴሌግራም ቻናሎችና ግሩፖች ላይ ባንኮች አጓጊ ሽልማቶችን አዘጋጅተዋል በማለት ቻናሎቹን እንዲቀላቀሉ እና ማስፈንጠሪያዎቹን ለብዙ ሰዎች እንዲያጋሩ በማድረግ እንደሚያታልሉ አጋርቷል ።

የገጻችን ተከታታዮች ባቀረቡልን ጥያቄ መሰረት በቴሌግራም ላይ ሽልማቶችን ያቀረበ እና ተመሳሳይ ይዘት ያለውን ቻናል አጣርተናል። ይህ በደቡብ ግሎባል ባንክ ስም የተከፈተው ቻናል ባስተላለፈው መልዕክት “ደቡብ ግሎባል ባንክ አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ እስከ መስከረም 30/2014 ዓ.ም የሚቆይ የቴሌግራም ገፅ ማነቃቂያ የሚሆን ሽልማቶች አዘጋጅቷል” ሲል ይነበባል።

ከዚህ በፊት ከነበሩት የቴሌግራም ማላለሎች በተለየ ሃቅቼክ መልዕክቶቹ በትክክልም የተላኩት ከባንኩ መሆኑን አረጋግጧል።   

        

ልጥፉ አራት የተለያዩ የሽልማት አይነቶችን አስቀምጧል። የመጀመሪያው ሽልማት ለ ሶስት እድለኛ አሸናፊዎች ዘመናዊ የሞባይል ቀፎዎችን ሲያስቀምጥ ካሉት ሌሎች የሽልማት አይነቶች መካካል ለአንድ ወር የሚቆይ የ ዲኤስቲቪ ዲኮደር ፓኬጅ ፣ የባንኩ የጎልደን ሜምበርሺፕ አካውንት እንዲሁም የ100 ብር የሞባይል ካርዶች ይገኙበታል።

ታድያ ይህን እድል መጠቀም የሚፈልጉ ሰዎች በመጀምሪያ ቻናሉን መቀላቀል ሲኖርባቸው በመቀጠልም ማስፈንጠሪያውን ለ50 ሰዎች በማጋራት ቻናሉን እንዲቀላቀሉ ማድረግ እንደሚኖርባቸው ምልክቱ ያስነብባል።

ይህን ነገር ለማጣራት ባደረግነው ጥረት መሰረት የደቡብ ግሎባል ባንክ ማርኬቲንግ እና ብራንድ ሲንየር ኦፊሰር የሆኑትን አቶ ተመስገን ፍቃዱን አነጋግርን “ የቴሌግራም ቻናሉ ትክክለኛ መሆኑን እና ለቴሌግራም ተጠቃሚዎችም የ100 ብር የሞባይል ካርድ ፣ የሞባይል ቀፎዎችን እና የዲኤስቲቪ ዲኮደሮችን እየሸለምን ነው” በማለት ገልጸውልናል።

በተጨማሪም የባንኩን የማርኬቲንግ እና የብራንድ ኦፊሰር የሆኑትን አቶ አስናቀ ወርቁ ሽልማቱ ትክክለኛ መሆኑን አረጋግጠውልናል። ወደተለያዩ የባንኩ ቅርንጫፎች በመደወል የመረጃውን ትክክለኛነት አረጋግጠናል።

ስለዚህ በደቡብ ግሎባል ባንክ ስም የቀረበው የአዲስ አመት የቴሌግራም መልዕክት ትክክል መሆኑን እንግልጻለን።           

Similar Posts