አንድ የፌስቡክ ፖስት ከ62,560 በላይ ተከታይ ባለው የፌስቡክ ገጽ ላይ ከተለጠፈበት ከጥር 17 ፤ 2014 ዓ.ም ጀምሮ ከ50 ጊዜ በላይ ተጋርቷል። የፌስቡክ ገጹ አብዛኛውን ጊዜ የአፋር ጉዳዮች ላይ የሚተነትን ሲሆን የፌስቡክ ፖስቱም ከ 1200 በላይ ግብረ መልሶችን ማግኘት ችሏል።

ከፖስቱ ጋር የተያያዘው ምስል በቁጥር በዛ ያሉ ጥይቶችን የሚያሳይ ሲሆን በአማርኛ የተያያዘው ጽሁፍ፣ “ጁንታው ማስረከብ ጀምረዋል አፋርም መረከብ ጀምረዋል። በሰሜናዊ ግንባር ህወሓትን በራሱ መሳርያ እየማረከ ድል ማድረጉን እየቀጠለ ነው” የሚል ነው። 

የፌስቡክ ፖስቱ ጁንታው ብሎ የሚጠራው የትግራይ ተዋጊ ሀይሎችን ሲሆን አፋር ደግሞ የትግራይ አጎራባች ክልል ነው። እንደሚታወቀው የአፋር ልዩ ሀይሎች እና ሚሊሽያ ከመከላከያ ሰራዊት ጋር በመጣመር ከህወሓት ጦር ጋር ውጊያ በማድረግ ላይ ይገኛሉ። ይሁን እንጂ የፌስቡክ ፖስቱ የጥይት ምስሎችን ያሳይ እንጂ ምስሉ የቆየ እና አሁን በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ካለው ግጭት ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም። ስለዚህ ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል። 

ጦርነቱ የጀመረው በጥቅምት 2013 ዓ.ም የህወሓት ሀይሎች በትግራይ ሰሜን ዕዝ በሚገኘው የመከላከያ ሰራዊት ላይ ጥቃት ከከፈቱ በኋላ ሲሆን ይህ ጦርነት ሶስት ሃገራቶችን ማለትም ኢትዮጵያ ኤርትራ እና ሱዳንን ሲጎዳ በሌላ በኩል ደግሞ በዋነኝነት ሶስት ክልሎችን ማለትም ትግራይ አማራን እና አፋርን ጎድቷል።

የፌደራሉ መንግስት በብሄራዊ መግባባት እና አንድነት ላይ የሚያተኩር አገር አቀፍ ውይይት ላይ ያለውን ፍላጎት ያስታወቀ ሲሆን በቅርቡም የፌደራሉ መንግስት የህወሓት አመራሮችን ጨምሮ ሌሎች የፖለቲካ እስረኞችን ክስ አቋርጧል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የአፋር ክልላዊ መንግስት  የህወሓት ሃይሎች ተከታታይ ጥቃት እያደረሱበት እንደሆነ አስታውቋል።    

ሀቅቼክ የምስሉን ትክክለኛነት ለማጣራት የጉግል ግልባጭ የምስል ፍለጋን ተጠቅሞ ያደረገው ፍለጋ ውጤት የሚያሳየው ምስሉ ከፈረንጆቹ 2014 ዓ.ም ጀምሮ ከተለያዩ ጽሁፎች ላይ አብሮ ታትሟል። ከዚህም በተጨማሪ ምስሉ በነሃሴ 2006 ዓ.ም በAMISOM (African Union Mission in Somalia) አማካኝነት የተያዘ መሳሪያን እንደሚያሳይ ሀቅቼክ አረጋግጧል። በዚህም መሰረት መረጃውን ለመደገፍ ከፓስቱ ጋር የተለጠፈውን ምስል ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል።  

Similar Posts