በጥር 28 ቀን 2015 ዓ.ም አንድ የትዊተር አካውንት ህገወጥ የጦር መሳርያዎች እና ጥይቶች በባህር ዳር ሀገረስብከት ሊቀጳጳስ እና የፓትርያርኩ ፅ/ቤት አመራር በሆኑት በአቶ አቡነ አብርሃም መኖርያ ቤት ውስጥ ተገኝተዋል በማለት ሶስት ምስሎችን አጋርቶ ነበር።

ይህ የትዊተር ፖስት በፖሊስ ፍተሻ ከአቡነ አብርሃም የመኖርያ ቤት ውስጥ አምስት ክላሽንኮቭ መሳርያዎች ከ235 ጥይት ጋር ተገኝቷል የሚል የመግለጫ ፅሁፍን አጋርቶ ነበር።  

ይህ ፅሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ይህ የትዊተር ፖስት ወደ አንድ መቶ ያህል ጊዜ መጋራት ችሎ የነበረ ሲሆን ወደ 20 ሺህ የሚጠጉ ሰዎች ተመልክተውታል።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ ምስሉን ተመልክቶ መረጃውን እንደማይደግፍ በማረጋገጥ ሀሰት ብሎታል። 

በጥር 14 ቀን 2015 ዓ.ም የቀድሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስትያን ሊቀ-ጳጳሳት ከቤተክርስትያኗ ሲኖዶስ እውቅና ውጭ የተለያዩ ጳጳሳትን ሾመዋል።

የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ-ጳጳስ እና ሁለት ሌሎች ጳጳሳት አንድ ላይ በመሆን ወደ 26 የሚጠጉ ኤጲስ-ቆጶሳትን በተለያዩ የኦሮሚያ እና የደቡብ ኢትዮጵያ አካባቢዎች ሾመዋል። ከዚህም በተጨማሪ በአቡነ ሳዊሮስ አማካኝነት ወደ 70 የሚጠጉ ጳጳሳት በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ የተለያዩ ደብሮች ላይ ተመድበው ነበር።

ከዚህ ሁኔታ በኋላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስትያን ሲኖዶስ በዚህ ጉዳይ ላይ አስቸኳይ ስብሰባን በመጥራት ከቤተክርስትያኗ እውቅና ውጭ የተሾሙትን ጳጳሶች እና በሹመቱ ላይ የተሳተፉትን በሙሉ አውግዛለች።

ከዚህም በተጨማሪ የቤተክርስትያኗ ሲኖዶስ እነ አቡነ ሳዊሮስን እና ሌሎች ጳጳሳትን የቤተክርስትያኗን ቀኖና በመተላለፋቸው ምክንያት ከአባልነት አስወግዳቸዋለች።    

ከጥቂት ቀናት በኋላ ከቤትክርስትያኗ ተለይተው የወጡት ሊቀጳጳሳትም በበኩላቸው ወደ 12 የሚጠጉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስትያን ሊቀጳጳሳትን በማውገዝ ከአባልነትም ማገዳቸውን አስታውቀው ነበር። 

የባህርዳር ሀገረስብከት እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤትክርስትያን ሊቀጳጳስ የሆኑት አቶ አቡነ አብርሃም ከቤትክርስትያኗ በተለዩት አዳዲሶቹ ሊቀጳጳሳት ከተገለሉት መካከል ናቸው።

በጥር 28 ቀን 2015 ዓ.ም የተጋራው ይህ የትዊተር ፖስት ህገወጥ የጦር መሳርያዎች እና ጥይቶች በባህር ዳር ሀገረስብከት ሊቀጳጳስ እና የፓትርያርኩ ፅ/ቤት አመራር በሆኑት በአቶ አቡነ አብርሃም መኖርያ ቤት ውስጥ ተገኝተዋል በማለት ሶስት ምስሎችን አጋርቶ ነበር። ከዚህም በተጨማሪ ይህ የትዊተር ፖስት በአቡነ አብርሃም የመኖርያ ቤት ውስጥ አምስት ክላሽንኮቭ መሳርያዎች ከ235 ጥይት ጋር ተገኝቷል የሚል የመግለጫ ፅሁፍን አጋርቶ ነበር።

ይሁን እንጂ ሀቅቼክ በዚህ የትዊተር አካውንት የተጋራውን መረጃ ተመልክቶ የተጋሩት ምስሎች የቆዩ እና መረጃውን የማይደግፉ እንደሆኑ አረጋግጧል። 

የመጀመርያው ምስል በአዲስ አበባ ቅንጡ የሆኑ ሆቴሎችን በሚያስተዋውቅ አንድ ድረ-ገፅ ላይ የተወሰደ ሲሆን እንደ ድረገፁ ከሆነ ምስሉ በአዲስ አበባ ቦሌ አካባቢ በሚገኝ እና ሸገር ሮያል የተሰኘ ሆቴል የውስጥ ክፍሎችን እንደሚያሳይ ተገልጿል።    

ሁለተኛው ምስል በመስከረም 20 ቀን 2013 ዓ.ም በአንድ የዜና ድረ-ገፅ ላይ ተጋርቶ የነበረ ሲሆን ከተጋራው ምስል ጋር ህንድ ከሩሲያ ጋር የ770,000 ክላሽንኮቭ መሳርያዎችን ለመግዛት የግዥ ስምምነት መፈፀሟን በሚያሳይ ፅሁፍ ስር አገኝቶታል።  

ሶስተኛው ምስል ደግሞ የአቡነ አብርሃም መሆኑ ይታወቃል። 

በዚህም ምክንያት ሀቅቼክ የትዊተር አካውንቱን ፖስት መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

Similar Posts