ከ75,000 በላይ ተከታዮች ያሉት አንድ የፌስቡክ ገጽ በሕዳር 19 ፤ 2014 ዓ.ም “ትናንት በካሳጊታ አፋር ግንባር የተማረኩ የብልጽግና ወታደሮች” የሚል ጽሁፍን በማያያዝ አንድ ምስልን አጋርቶ ነበር። ይህ ጽሁፍ ለንባብ እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የፌስቦክ ልጥፉ ከ800 በላይ ግብረ መልስ አግኝቷል።

ምስሉ በሌሎች ገጾች እና የዜና አውታሮች በተለያየ አውድ የቀረበ ሲሆን ሀቅቼክ ምስሉን መርምሮ ሀሰት ብሎታል።

 

ከጥቅምት 2013 ዓ.ም ጀምሮ በትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር (ህወሓት) እና በፌደራል መንግስቱ መካከል ወታደራዊ ግጭት ቀጥሏል። በግንቦት 2013 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ የፌደራሉ መንግስት ከትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በቀረበለት ጥያቄ መሰረት ድንገተኛ የአንድ ወገን የተኩስ አቁም ስምምነትን በማድረግ ሁሉንም የመከላከያ እና የክልል ልዩ ሃይሎችን ከክልሉ ዋና ዋና ቦታዎች አስወጥቷል። 

ከዚያ በኋላ የህወሓት ሃይሎች ራሳቸውን በማጠናከር ወደክልሉ ደቡባዊ አቅጣጫ በመንቀሳቀስ አጎራባች በሆኑት የአማራ እና አፋር አካባቢዎች ላይ ጥቃት ሰንዝረዋል። በሓምሌ 29 ፤ 2013 ዓ.ም የህወኃት ሃይሎች በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ አካባቢ የምትገኘውን የላሊበላ ከተማን እና አካባቢውን ተቀጣጥረዋል። 

በሕዳር 13 ፤ 2014 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ጦርነቱን በግምባር ሆነው ለመምራት መወሰናቸውን ተከትሎ የተለያዩ የማጥቃት እና የመልሶ ማጥቃት የጦርነት ዜናዎች እየተሰማ ይገኛል። በሕዳር 17 ፤ 2014 ዓ.ም በፌደራል መንግስት የሚመራው ጥምር ሀይል ካሳጊታን መልሶ መያዙን እና ወደ ቡርቃ እና ባቲ አካባቢ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አሳውቀዋል። 

ከፌስቡክ ልጥፉ ጋር የተያያዘው ምስል የጉግል ተገላቢጦሽ ምስል ፍለጋ እንደሚያሳየው ከሆነ ምስሉ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጋራው ትግራይ ፕሬስ በሚባል የፌስቡክ ገጽ በነሃሴ 2013 ዓ.ም ነበር።   

ስለሆነም ምስሉ ማስተላለፍ ከፈለገው መልዕክት ጋር የተሳሳተ ግንኙነት ስላለው ሀቅቼክ ሀሰት ብሎታል።

Similar Posts